አሜሪካ ከእስራኤል ሚሳየል ማክሸፊያ የመግዛት እቅድ እንዳላት አስታወቀች

መሳሪያው እንደ አውሮፓውያኑ ከ2011 ጀምሮ እስራኤል ውስጥ ጥቅም ላይ ውሏል

የፎቶው ባለመብት, AFP

የምስሉ መግለጫ, መሳሪያው እንደ አውሮፓውያኑ ከ2011 ጀምሮ እስራኤል ውስጥ ጥቅም ላይ ውሏል

የአሜሪካ ጦር ሰራዊት ከእስራኤል ሊገዛ ያሰበው ራዳርን ተጠቅሞ ሚሳየሎችን በማጨናገፍ የጠላትን ጥቃት የሚመልስና እንደ አውሮፓውያኑ ከ2011 ጀምሮ በስራ ላይ የዋለን መሳሪያ ነው።

የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር መሳሪያው ሙከራን መሰረት ባደረገ መልኩ እንዲሁም ከአገሪቱ የረዥም ጊዜ ፍላጎት አንፃር ጥቅም ላይ እንደሚውል አስታውቋል።

የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ናታኒያሁ ደግሞ የአሜሪካ መሳሪያቸውን መግዛት ለአገራቸው እስራኤል ትልቅ ስኬት እንደሆነ ተናግረዋል።

"ይህ ከአሜሪካ ጋር ያለን አጋርነት እየጨመረ የመሆኑ፤ እንዲሁም እስራኤል በአለም አቀፍ ደረጃ ቦታዋ ከፍ እያለ የመምጣቱ መገለጫ ነው" ብለዋል።

የእስራኤል ባለስልጣናት መሳሪያው በማንኛውም የአየር ሁኔታ የሚሰራና ተንቀሳቃሽ እንደሆነና ውጤታማነቱም እስከ 90 በመቶ እንደሚሄድ ይናገራሉ።

የእስራኤል መከላከያ የሚያስተዳድረውና ራፋይል የተሰኘው ድርጅት ይህንን መሳሪያ መስራት አመታት ወስዶበታል።

ለዚህ መሳሪያ መሰራት አሜሪካ ድጋፍ ስታደርግ የነበረ ሲሆን የተወሰኑት የመሳሪያው ግብአቶች ከአሜሪካ ድርጅቶች የሄዱም ነበሩ።

የእስራኤል መከላከያ ሚኒስቴር በፅሁፍ እንዳወጣው መረጃ አሜሪካ የመሳሪያውን ግዥ የፈፀመችው 'ለአስቸኳይ ፍላጎት' ነው።

የአሜሪካ ሰራዊቱ ኮሎኔል ፓትሪክ ሲበር ደግሞ መሳሪያው ሙከራን መሰረት ባደረገ መልኩ በተልእኮ ላይ ያለን የአሜሪካ ጦር ለመከላከል አገልግሎት ላይ እንደሚውል ተናግረዋል።