የህንድ ፊልም አፍቃሪዎች ወተት እየሰረቁ ነው

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በደቡባዊ ህንድ ታሚል ናዱ ግዛት የሚገኙ ወተት ሻጮች መጠነ ሰፊ የወተት ዝርፊያ እየተካሄደባቸው መሆኑን ለፖሊስ ገልጸዋል።
ህንድ ውስጥ በአንዳንድ ሃይማኖታዊ ሥርዓቶች ላይ ለመልካም ዕድል እየተባለ አማልክት ላይ ወተት ማፍሰስ የተለመደ ነው። ታዲያ ይህንን ባህል በመከተል በግዛቲቱ የሚገኙ የፊልም አፍቃሪዎች የሚወዱት ፊልም ስኬታማ እንዲሆን በማለት ግዙፍ ማስታወቂያዎች ላይ ወተት ማፍሰስ ከጀመሩ ሰነባብተዋል።
ወተቱን የሚያመጡት ደግሞ ከሻጮች በመስረቅ መሆኑ ነገሩን ትንሽ ለየት ያደርገዋል። የወተት ሻጮቹ በፊልም አፍቃሪዎቹ ምክንያት ከባድ ኪሳራ እንደደረሰባቸው በምሬት ለፖሊስ አስታውቀዋል።
የወተት ሻጮች ማህበሩ ፕሬዝዳንት ደግሞ ይህ ሥነ ሥርዓት የሚካሄደው ለአማላክት እንጂ ለፊልም ተዋናዮች አይደለም ሲሉ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።
ፖሊስ አፋጣኝ እርምጃ እንዲወስድ ማህበሩ የጠየቀ ሲሆን ፖሊስም አታስቡ እርምጃ እወስዳለሁ ብሏቸዋል።
'ፓላቢሼካም' በመባል የሚታወቀው ሥነ ሥርዓት የሚካሄደው ፊልሙን ለማስተዋወቅ በተሰቀሉ ግዙፍ ማስታወቂያዎች ላይ እና የፊልም ተዋናዮቹ ትንንሽ ምሥሎች ላይ ወተት በማፍሰስ ነው።
ይህ ለ20 ዓመታት ሲደረግ ነበር ሥነ ሥርዓት አድናቂዎቹ የወደዱት ፊልም ስኬታማ እንዲሆን ያደርገዋል ተብሎ ይታመናል።
በታሚል ናዱ ግዛት የሚገኙት የወተት አከፋፋዮች በትልልቅ መኪናዎች የሰበሰቧቸውን ወተቶች በየሱቆቻቸው ደጃፍ ላይ በማስቀመጥ ነው የሚሸጧቸው።
እነዚህ ለማዳ የተባሉት የወተት ቀበኞች ታዲያ አሳቻ ሰዓት በመጠበቅና ባለሱቆቹ ሲዘናጉ የቻሉትን ያህል ወተት ተሸክመው ይሮጣሉ፤ አልያም በመኪናቸው ይዘው ይሰወራሉ።
ታዋቂው የቦሊዉድ ፊልም ተዋናይ ሲላምባርሳን አዲስ የለቀቀው ፊልሙ ተወዳጅ እንዲሆንለት አድናቂዎቹ በየመንገዱ የተሰቀሉ ማስታወቂያዎችን ወተት በወተት አድርገዋቸዋል። እሱም ወተት እንዲያፈሱለት የተማጽኖ መልእክት አስተላልፎ ነበር።
ታዲያ ታዋቂው ፊልም ተዋናይ የለቀቀው ተንቀሳቃሽ ምሥል በታሚል ናዱ ግዛት ብዙ ተቀባዮችን ማግኘቱ የወተት ሻጮችን ሕይወት ከባድ አድርጎታል እየተባለ ነው።












