በጋዛ የእስራኤልና የፍልስጥኤም ግጭት እየተባባሰ ነው

በጋዛ ጥቃት የተሰነዘረበት አውቶቡስ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, አውቶቡስ ላይ በተሰነዘረ ጥቃት አንድ እስራኤላዊ በፅኑ ተጎደቷል

እስራኤል እሁድ እለት በጋዛ ያደረገችውን ስውር ወታደራዊ ተልኮ ተከትሎ ሰባት ታጣቂዎችና አንድ እስራኤላዊ ወታደር ሞተዋል። ታጣቂዎቹ 300 ሮኬቶችንና ሞርታሮችን እስራኤል ላይ አስወንጭፈዋል።

በተለይም አንደኛው ሮኬት አወቶብስ መትቶ በአቅራቢያው የነበረ ወታደርን በፅኑ ማቁሰሉ ተዘግቧል።

በአፀፋው ደግሞ እስራኤል የሃማስና የኢዝላሚክ ጂሃድ ይዞታ ናቸው ባለቻቸው ቦታዎች ላይ ከ70 በላይ የአየር ጥቃቶችን ፈፅማለች። በዚህም ሶስት ፍልስጥኤማዊያን የተገደሉ ሲሆን ሁለቱ ወታደሮች ናቸው።

ሃማስ የሚያስተዳድረው ይዞታ ጤና ጥበቃ በጥቃቱ ዘጠኝ ሰዎች መጎዳታቸውን አስታውቋል። በእስራኤል በኩልም በተመሳሳይ አስር ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል ተብሏል።

አሽኬሎን በተባለ የእስራኤል ከተማ መኖሪያ ቤት ላይ በደረሰ የሮኬት ጥቃት አንድ እስራኤላዊ መሞቱንም የእስራኤል መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

የእስራኤሉ ሜጀር ጀነራል ካሚል አቡ ሩካን ሃማስ ቀይ መስመር እያለፈ በመሆኑ እስራኤል በከባዱ አፀፋውን እንደምትመልስ አስጠንቅቀዋል።

በፈረንሳይ ጉብኝት ላይ የነበሩት የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ ለአስቸኳይ ስብሰባ ጉብኝታቸውን አቋርጠው ወደ አገራቸው ተመልሰዋል።

እሁድ እለት እስራኤል በጋዛ ያደረገችውን ስውር ወታደራዊ ተልእኮ ተከትሎ ከተገደሉ መካከል የሃማስ ኮማንደርና የእስራኤል ወታደር ይገኙበታል።