ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በግብጻዊው የሊቨርፑሉ አጥቂ ሞሐመድ ሳላህ ቅርጽ የተሰራው ሃውልት መሳለቂያ ሆኗል
ምትሃተኛው የሊቨርፑል እና የግብጽ ብሔራዊ ቡድን የፊት መስመር ተጫዋች ሞሃመድ ሳላህ ቅርጽ ተሰራ የተባለው ሃውልት የበርካቶች መቀለጃ ሆኗል።
ይህ የጥበብ ሥራ በግብጽ ሻርም አል-ሼክህ ስታዲየም ባሳለፍነው እሁድ ነበር ለህዝብ ይፋ የተደረገው።
የፊት መስመር ተጫዋቹ ጎል ካስቆጠረ በኋላ ደስታውን የሚገልጽበትን ሁኔታን ያሳያል ተብሏል።
ቅርጹ ሞ ሳላን ስለመምሰሉ ግን ብዙዎች እየተጠራጠሩ ነው።
በሞ ሳላህ ምስል ተሰራ የተባለው ሃውልት ከዚህ ቀደም በክርስቲያኖ ሮናልዶ ቅርጽ ተሰራ ከተባለው ሃውልት ጋር ሰዎች እያነጻጸሩት ይገኛሉ።
ይህን የጥበብ ሥራ የሰራችው ቀራጺዋ ማያ አብደላህ ለግብጽ መገናኛ ብዙሃን ''ይህን ልዩ የሆነ'' የጥበብ ሥራ የሰራሁት ሞሐመድ ሳላህ ለግብጻውያን ወጣቶች የስኬታማነት ምልክት አድርጌ ስለምወስደው ነው ብላለች።
ማያ በፌስቡክ ገጿ ላይ ባሰፈረችው ጽሑፍ የቅርጹ የመጨረሻ ውጤት ከመጀመሪያ እንደተለየ ገልጻ ''ሰዎች የሚሰጡት አስተያየት ትህትናና ክብር የተሞላበት እንደሚሆን ተስፋ አለኝ'' ብላለች።
ሞ ሳላህ በትዊተር ገጹ ላይ ቅርጹን በተመለከተ ተሳልቋል።
የሞ ሳላህ ቅርጽ ይፋ የተደረገው የግብጽ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታ አልሲሲን ጨምሮ በሺዎች የሚቆጠሩ ታዳሚዎች በተገኙበት ነው።