የሱዳን ጦር መሪ መሣሪያ ታጥቀው በአንድ ተንቀሳቃሽ ምስል ላይ ታዩ

የሱዳን ጦር ሠራዊት ዋና አዛዡ ሌተናንት ጄኔራል አብደል ፋታህ አል-ቡርሃን ከወታደሮቻቸው ጋር ሆነው የሚታዩበትን ምስል ለቋል።

የጦሩ መሪ አል-ቡርሃን አድራሻው ባልታወቀ አንድ የኻርቱም አካባቢ ወታደሮቻቸው በደስታ ከበዋቸው ታይተዋል።

ረቡዕ ዕለት የተለቀቀው የ23 ሰከንድ ምስል እንደሚያሳየው ጀኔራል ቡርሃን የጦር መሣሪያ ታጥቀዋል።

ወታደራዊ መለዮ የለበሱት ጄኔራሉ በደስታ ያጀቧቸውን ወታደሮች እየዞሩ ሲጨብጡ ይታያሉ።

ጦር ሠራዊቱ “ተዋጊው - የታጣቂ ኃይሉ ጦር አዛዥ - ጦር ሜዳ ላይ በወታደሮቻቸው ተከበው” በሚል ርዕስ ተንቀሳቃሽ ምስሉን ያጋራው።

ይህ ተንቀሳቃሽ ምስል፤ በሱዳን ጦርና በተቀናቃኙ የፈጥኖ ደራሽ ኃይል መካከል ባለፈው ወር ግጭት ከተቀሰቀሰ በኋላ የወጣ የመጀመሪያው ምስል ነው።

ነገር ግን ግጭቱ የተቀሰቀሰ ሰሞን ጀኔራል አል-ቡርሃን ሌሎች ወታደራዊ አመራሮች የሱዳን ዋና መዲና ኻርቱም ውስጥ አድራሻው ከማይታወቅ ሕንፃ ወደታራዊ ትዕዛዝ ሲሰጡ ይታዩ ነበር።

የሱዳን ጦር መሪው አል-ቡርሃንም ሆነ ሄምቲ በተሰኘ ቅፅል ስማቸው የሚታወቁት የየፈጥኖ ደራሽ ኃይል አዛዥ ጀኔራል ሞሐመድ ሃምዳን ደጋሎ የወታደሮቻቸውን ሞራል ከፍ ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ ነው።

ሄምቲ በቅርቡ ከአንድ አድራሻው በማይታወቅ የኻርቱም ሥፍራ ሆነው ተመሳሳይ ይዘት ያለው ምስል ለቀው ነበር። አልፎም በቅርቡ ተገድለዋል የሚባለው ወሬ ሐሰት መሆኑን የሚያትት የድምፅ መልዕክት ልከዋል።

በጀኔራል ቡርሃን እና ሄምቲ መካከል ባለው የሥልጣን ሽኩቻ ምክንያት እንደተቀሰቀሰ የሚነግረለት የሱዳን ግጭት ሁለተኛ ወሩን ይዟል።

እስካሁን በግጭቱ ምክንያት ከ800 በላይ ሰዎች ሕወታቸው ሲያልፍ በርካቶች ደግሞ ቆስለዋል።