የቀድሞው የሲአይኤ አባል የ40 ዓመት እስር ተፈረደበት

ሲአይኤ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የቀድሞው የሲአይኤ ባልደረባ ምሥጢራዊ መረጃ መጥለፊያ መሣሪያዎችን አሾልኮ ለዊኪሊኪስ በመስጠቱ የ40 ዓመት እስራት ተፈረደበት።

ጆሹዋ ሹልተ የተባለው የቀድሞ የሲአይኤ ባልደረባ የልጆች ጥቃትን የሚያሳዩ ምስሎችን ይዞ መገኘት በሚል ወንጀልም ጥፋተኛ ሆኖ ተገኝቷል።

ሲአይኤ “ቮልት 7” ሲል የሚጠራውን እና ስማርት ስልኮችን ለመጠለፍ እንዲሁም ድምጽ ለመስማት የሚያስችለውን መገለገያን በተመለከተ መረጃ አሾልኮ አውጥቷል የሚል ክስ ዐቃቤ ሕግ አቅርቦበታል።

ድርጊቱንም በዩናይትድ ስቴትስ ታሪክ ውስጥ ከታዩት እጅግ በጣም “አስፈሪ” ከሆኑት አንዱ ነው ተብሏል።

የ35 ዓመቱ ሹልተ በ2017 (እአአ) 8 ሺህ 761 ሰነዶችን ለዊኪሊክስ አጋርቷል። ይህም በሲአይኤ ታሪክ ትልቁን መረጃ አሳልፎ የመስጠት ጥሰት ነው ሲል የአሜሪካ የፍትህ ሚኒስቴር አስታወቋል።

ግለሰቡ ክሱን ውድቅ ቢያደርግም በኒውዮርክ በተደረጉ ሦስት የተለያዩ የፌዴራል ችሎቶች በተለያዩ ክሶች ተፈርዶበታል።

ሐሙስ ዕለት ደግሞ በስለላ፣ በኮምፒውተር ጠለፋ፣ ፍርድ ቤትን በመድፈር፣ ለኤፍቢአይ የውሸት መረጃዎችን በመስጠት እና በልጆች ላይ የሚፈጸም ጥቃት የሚያሳዩ ምሥሎችን በመያዝ ተከሷል።

“ጆሹዋ ሹልተ በአሜሪካ ታሪክ ውስጥ እጅግ አሰቃቂ እና ከባድ የስለላ ወንጀሎችን በመሥራት አገሩን ከድቷል” ሲሉ የአሜሪካ ዐቃቤ ሕግ ዴሚያን ዊሊያምስ ተናግረዋል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

በችሎቱ ላይ የተሰጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ሹልተ በሴንተር ፎር ሳይበር ኢንተለጀንስ ውስጥ በሶፍትዌር ባለሙያነት ተቀጥሮ ይሠራ ነበር። ድርጅቱ በአሸባሪ ድርጅቶች እና በውጭ መንግሥታት ላይ የሳይበር ስለላ ሥራ የሚያከናውን ነው።

ዐቃቤ ሕግ በ2016 (እአአ) የተወሰደውን መረጃ ለዊኪሊክስ እንዳስተላለፈ እና በዚህ ውስጥ ስላለው ሚና ለኤፍቢአይ ወኪሎች የተሳሳተ መረጃ ሰጥቷል ብሏል።

በሥራ ቦታ በተፈጠረው አለመግባባት የተነሳ የተበሳጨ ይመስላል ሲሉም አክለዋል።

ሹልተ ሥራዎቹን በቀነ-ገደቦች ለማድረስ ካለመቻሉም በላይ እንደ አሜሪካ ረዳት ዐቃቤ ሕግ ማይክል ሎካርድ ገለጻ ከሆነ አንዱ ፕሮጀክቱ ከታቀደለት ጊዜ በጣም ዘግይቶ ስለነበር “ቀርፋፋው” የሚል ቅፅል ስም እንዳገኘ ተናግረዋል።

በደል ፈጽመውብኛል ያላቸውን ሰዎች ለመቅጣት እንደሚፈልግ ተናግሮ “የበቀል እርምጃ በመውሰድ በአሜሪካ ብሔራዊ ደኅንነት ላይ ከፍተኛ ጉዳት አድርሷል” ብሏል ዐቃቤ ሕግ።

ዊኪሊክስ ከአውሮፓውያኑ 2017 ጀምሮ ነው መረጃዎቹን ይፋ ማድረግ ያደረገው።

መረጃው “ፍጥነት እና በከፍተኛ ደረጃ ሲአይኤ በአሜሪካ ጠላቶች ላይ መረጃን የመሰብሰብ አቅሙን ጎድቶታል። የሲአይኤ ሠራተኞችን፣ ፕሮግራሞችን እና ንብረቶችን በቀጥታ አደጋ ላይ ጥሏል። ሲአይኤም በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር እንዲያወጣ አድርጓል” ብለዋል።

ዊኪሊክስ መረጃውን ይፋ ካደረገ በኋላ ኤፍቢአይ ሹልተን በተደጋጋሚ ቃለ መጠይቅ ቢያደርግለትም ጥፋተኛ አለመሆኑን ተናግሯል።

ዐቃቤ ሕግ በሚኖርበት አፓርታማ ላይ ባደረገው ፍተሻ “በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ የልጆች ወሲባዊ ጥቃት የሚያሳዩ ምሥሎች” መገኘታቸውን ተናግሯል።

ሹልተ ከታሰረ በኋላም ተጨማሪ መረጃዎችን ለማስተላለፍ እንደሞከረም አክለዋል። ስለ ሲአይኤ የሳይበር ቡድኖች መረጃ ለመስጠት በድብቅ ወደ ማረሚያ ቤት ባስገባው ስልክ ለጋዜጠኛ ለመላክ ከመሞከር ባለፈ ራሱ በከፈተው እና ጄሰን ቡረን በተባለ የትዊተር መረጃዎችን ለማሰራጨት ሞክሯል።

ግለሰቡ ከአውሮፓውያኑ 2018 ጀምሮ በእስር ቤት ይገኛል።