ቴን ሃግ ከማንችስተር ሽንፈት በኋላ ራሽፈርድ ልደት መደገሱ ተቀባይነት የለውም አሉ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ኤሪክ ቴን ሃግ ቡድናቸው በማንቸስተር ደርቢ ከተሸነፈ በኋላ የፊት መስመር ተጫዋቻቸው ልደት መደገሱ ተቀባይነት የለውም አሉ።
ማርከስ ራሽፈርድ ቡድኑ ዩናይትድ በሜዳው እና በደጋፊው ፊት በማንቸስተር ሲቲ 3-0 ከተሸነፈ ከሰዓታት በኋላ የልደት በዓሉን ለማክበር በአደባባይ ታይቷል።
እሁድ ዕለት የነበረው የልደት ዝግጅት ቀድሞ የታቀደ ነበር። ዩናይትድ ‘አሳፋሪ’ በተባለ ሁኔታ በኦልትራፈርድ ሽንፈትን ቢከናነብም ራሽፎርድም ቀድሞ ካዘጋጀው ድግስ መቅረትን አልመረጠም።
የፊት መስመር ተጫዋቹ ከሽንፈቱ በኋላ ለልደት በዓሉ በማንቸስተር ከተማ የባለጸጎች መዋያ ከሆነ የምሽት መዝናኛ ስፍራ ታይቷል።
አሰልጣኝ ቴን ሃግ "ይህ ተቀባይነት የለውም። ስለ ልደት ፓርቲው ሰምቻለሁ። በጉዳዩ ላይ አውርተን ይቅርታውን ጠይቋል” ብለዋል።
ዕሁድ ዕለት 26 ዓመት የደፈነው ራሽፈርድ በልደት ዝግጅቱ ምክንያት ቅጣት ይጠብቀው እንደሆነ ቴን ሃግ ከመግለጽ ተቆጥበዋል።
ይሁን እንጂ ተጫዋቹ በተግባሩ ምክንያት ከቡድኑ እንደማያገሉት ቴን ሃግ ተናግረዋል።
ከልደት ፓርቲው ማግስት ሰኞ ጠዋትም በሰዓቱ ለልምምድ ተገኝቷል።
ማንቸስተር ሲቲ በሃላንድ እና ፎደን ታግዞ በኦልድ ትራፈርድ ዩናይትድን መርታቱ ይታወሳል።
የፔፕ ጉዋርዲዮላ ቡድን ከጨዋታው መጀመሪያ አንስቶ በኳስ ቁጥጥር ከተቀናቃኛቸው ልቀው ታይተው ነበር።
በሺዎች የሚቆጠሩ የዩናይትድ ደጋፊዎች ጨዋታው ከመገባደዱ በፊት ስታድየሙን ለቀው የወጡ ሲሆን፣ ይህም ክለቡ ያለበት ቀውስ ማሳያ ነውም ተብሏል።












