በግድቡ ጉዳይ ትራምፕ ኢትዮጵያን ከድተዋል?

የፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተቺዎች እንደሚሉት፤ ፕሬዚዳንቱ ለዘመናት የአሜሪካ ወዳጆች በሆኑት ኢትዮጵያ እና ግብፅ መካከል ታላቁ የሕዳሴ ግድብን በተመለከተ ውጥረት ቀስቅሰዋል።

ይህም በአሜሪካ እና በአፍሪካ የዲፕሎማሲ ታሪክ ትልቁ የትራምፕ ስህተት ነው ይላሉ።

ትራምፕ ከቀናት በፊት ግብፅ "ግድቡን ልታፈነዳው ትችላለች" ማለታቸው ይታወሳል።

ጥር ላይ ፕሬዚዳንቱ "ስምምነት መፍጠር ችያለሁ፤ ከባድ ጦርነትም አስቁሜያለሁ" ብለው የኖቤል የሰላም ሽልማት እንደሚገባቸው መናገራቸው ይታወሳል።

ነገር ግን ተሸላሚ የሆኑት ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድ ነበሩ ።

ትራምፕ የኖቤል የሰላም ሽልማት እንደሚገባቸው ሲናገሩ ጉዳዩን ግልፅ ባያደርጉትም፤ በግብፁ ፕሬዘዳንት አብዱልፈታህ አል-ሲሲ ጥሪ መሠረት በኢትዮጵያ እና በግብፅ መካከል ጣልቃ ስለመግባታቸው እየተናገሩ እንደነበረ ይታመናል።

ትራምፕ በአንድ ወቅት አብዱልፈታህ አል-ሲሲን "የኔ ምርጡ አምባገነን" ማለታቸው አይዘነጋም።

ግብፅ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ "ለደህንነቴ ያሰጋኛል" ትላለች። ሱዳንም የግብፅን ያህል ባይሆንም ስጋቱን ትጋራለች።

በሌላ በኩል ኢትዮጵያ የኃይል አመንጪውን ግድብ አስፈላጊነት አስረግጣ ትገልጻለች።

ኢትዮጵያውያን ትራምፕን ጠልተዋል?

ኬንያ የሚገኘው የአፍሪካ ቀንድ የጸጥታ ጉዳይ ተንታኝ ረሺድ አብዲ እንደሚለው፤ በግድቡ ዙሪያ ኢትዮጵያ እና ግብፅን ለማደራደር አሜሪካ ጣልቃ መግባቷ የሁለቱን አገሮች ውጥረት አባብሷል።

"ኢትዮጵያ በግድቡ አቅራቢያ የጸጥታ ኃይሏን እያጠናከረች ነው። ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልልን ከበረራ ውጪ ማድረጓ አንዱ ማሳያ ነው። በግድቡ ዙሪያ በረራ የሚያግድ መሣሪያም ተገጥሟል። ግብፅ የወታደራዊ ቅኝት በረራ ልታደርግ እንደምትችል ከመስጋት የመነጨ ሊሆን ይችላል" ይላል።

ተንታኙ እንደሚናገረው፤ ትራምፕ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ እንዴት እንደሚሠራ የሚገነዘቡ አይመስልም።

"በንግዱ ዓለም እንደሚደረገው ስምምነት ላይ መድረስ ይቻላል የሚል የተዛባ አመለካከት አላቸው። የውጪ ጉዳይ መያዝ ያለበትን ጉዳይ ግምዣ ቤት ድርድሩን እንዲመራ ያደረጉትም ለዚህ ነው። ከመነሻውም መጥፎ የነበረውን ሁኔታም አባብሶታል" ሲልም ረሺድ ያስረዳል።

ኢትዮጵያ ከግብፅ እና ከሱዳን ጋር ያለው ድርድር ሳይቋጭ ግድቡን ለመሙላት በመወሰኗ አሜሪካ የ100 ሚሊዮን ዶላር እርዳታ ማጠፏ ተዘግቧል።

ረሺድ "ኢትዮጵያ አሜሪካ እንደከዳቻት ይሰማታል። ብዙ ኢትዮጵያውያን ትራምፕን የጥላቻ ምልክት አድርገውታል" በማለት ሁኔታውን ይገልጻል።

የዴሞክራት እጩው ጆ ባይደን እንዲያሸንፉም የበርካታ ኢትዮጵያውያን ምኞት ነው።

አሜሪካ የሚገኘው ሴንተር ፎር ግሎባል ዴቨሎፕመንት ውስጥ የፖሊሲ አጥኚ ደብሊው ጉዬ ሙር እንደሚሉት፤ የትራምፕ አስተዳደር እስራኤልና የአረብ ሊግ አገራት መካከል ሰላም መፍጠር ስለሚፈልግ ከግብፅ ጎን መቆሙ የሚጠበቅ ነው።

የትራምፕ ዲፕሎማሲ

ግብፅ ከእስራኤል ጋር ዘመናት ያስቆጠረ ዲፕሎማሲያዊ ትስስር አላት። ትራምፕ የአረብ ሊግ አገራት ለእስራኤል እውቅና እንዲሰጡ ጥረት እያደረጉ ስለሆነ አብዱልፈታህ አል-ሲሲን ማስቀየም አይፈልጉም።

ሙር እንደሚናገሩት፤ የትራምፕ አስተዳደር በግድቡ ዙርያ ለግብፅ የወገነውም በዚህ ምክንያት ነው።

ትራምፕ ሱዳንን በተመለከተ የደረሱበት ውሳኔ የአረቡን አገራት ከእስራኤል ጋር ለማስስማት የሚያደርጉት ጥረት አንድ አካል ነው።

ሱዳን ከእስራኤል ጋር ስምምነት ለማድረግ ወስናለች።

በእርግጥ የአገሪቱ ተጠባባቂ የውጪ ጉዳይ ሚንስትር ውሳኔው ገና በሕግ አውጪ መጽደቅ እንዳለበት ቢናገሩም፤ ሱዳን እንደ ጎርጎሮሳውያኑ 1967 ላይ የአረብ ሊግ አገራት ውይይት ማስተናገዷ መዘንጋት የለበትም።

በውይይቱ "ከእስራኤል ጋር መቼም ሰላም አይፈጠርም። መቼም ቢሆን ለእስራኤል እውቅና አይሰጥም። ድርድርም አይካሄድም" ተብሎም ነበር።

ሱዳን ከእስራኤል ጋር ለመስማማት በመፍቀዷ ትራምፕ ሽብርን ከሚድፉ አገሮች ዝርዝር እንደሚያስወጧት ተናግረዋል። ይህም ለምጣኔ ሀብቷ ማገገም የሚረዳ ድጋፍ እንድታገኝ ያግዛታል።

ትራምፕ በድጋሚ ከተመረጡ ኢትዮጵያ ግድቡን በተመለከተ ሱዳን እና ግብፅ ላላቸው ስጋት አንዳች መልስ እንድትሰጥ ጫና እንደሚያደርጉ ይጠበቃል።

አጥኚው እንደሚሉት፤ ሱዳን ሽብርን ከሚደግፉ አገሮች ዝርዝር ከወጣች የትራምፕ አስተዳደር በምላሹ የሚጠብቀው ነገር አለ።

"ከእስራኤል ጋር ስምምነት የመፍጠር ጉዳይ የሱዳን ማኅበረሰብን የከፋፈለ ነው። መንግሥት የራሱ የጸጥታ ጥያቄዎች እያሉበት ይህን ውሳኔ ማሳለፉ ችግር ሊያስከትል ይችላል" ብለዋል።

ከቻይና ጋር ያለው ውጥረት

ትራምፕ አፍሪካን በተመለከተ የሚያራምዱት ፖሊሲ፤ በአሜሪካ እና በቻይና መካከል የሚካሄድ 'አዲሱ ቀዝቃዛ ጦርነት' ነው ሲል ረሺድ ይገልጸዋል።

ለምሳሌ ቻይና ከግዛቷ ውጪ የመጀመሪያውን ወታደራዊ መቀመጫ የከፈተችው በጅቡቲ ነው። ማዕከሉ የሚገኘው አሜሪካ የሶማሊያ ታጣቂዎች ላይ የአየር ጥቃት ለመሰንዘር ያቋቋመችው ማዕከል አቅራቢያ ነው።

በቅርቡ የአሜሪካ ተዋጊ ጀቶች ለማረፍ ሲሞክሩ፤ ቻይና የአሜሪካውያን ወታደሮችን እይታ የሚጋርድ መሣሪያ መሞከሯን ረሺድ ያጣቅሳል።

"የትራምፕ አስተዳደር ጸረ ቻይና ፖሊስ ያራምዳል" የሚለው ተንታኙ ሁኔታው ለአፍሪካ ቀንድ አስቸጋሪ መሆኑንም ያስረዳል።

ቻይና አፍሪካ ውስጥ ያላትን የንግድ የበላይነት ለመቀልበስ፤ የትራምፕ አስተዳደር 'ፕሮስፔሪቲ አፍሪካ ኢን 2018' የተባለ ፖሊሲ ነድፏል።

በአፍሪካ እና በአሜሪካ መካከል የሚካሄደውን ንግድ በእጥፍ የማሳደግ እቅድ አለ።

አምና የአሜሪካ መንግሥት የንግድ ተቋሞች አፍሪካ ውስጥ እንዲሠሩ የገንዘብ ድጋፍ የሚሰጥበት አሠራር ዘርግቷል።

ሙር እንደሚሉት፤ የአሜሪካ ድርጅቶች ከቻይና ተቋሞች ጋር መወዳደር አልቻልንም ብለው ቅሬታ ስላሰሙ የገንዘብ ድጋፍ ለመስጠት ተወስኗል።

"የአይቲ ዘርፍ እንደ ማሳያ ቢወሰድ፤ 70 በመቶ የአፍሪካ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ የተመሠረተው በቻይና ድርጅቶች ላይ ነው" ሲሉ ያብራራሉ።

የአፍሪካ ሕብረትን ማጣጣል

የትራምፕ አስተዳደር በ2025 የሚያበቃውን ከ30 በላይ የአፍሪካ አገሮች ተጠቃሚ እንዲሆኑበት ታስቦ በአሜሪካ ለአፍሪካውያን የተሰጠው ከታሪፍና ከቀረጥ ነፃ የገበያ ዕድል (አፍሪካ ግሮዝ ኤንድ ኦፖርቹኒቲ አክት-አጎዋ) የመሰረዝ እቅድ አለው።

ለአፍሪካ ምርቶች የአሜሪካን ገበያ ክፍት የሚያደርገው ስምምነት የተፈረመው በቢል ክሊንተን ነበር።

አሜሪካ አሁን ላይ ትኩረቷ የሁለትዮሽ የንግድ ስምምነት እንደሆነ ሙር ይናገራሉ። ለምሳሌ ከኬንያ ጋር ንግግር እየተካሄደ ነው።

ኬንያ፤ የቻይና 'ቤልት ኤንድ ሮድ ኢኒሽየቲቭ' አካል እንደሆነች ይታወቃል።

ስምምነቱ ቻይናን ከአፍሪካ ጋር በንግድ የሚያስተሳስርና የቻይና ዓለም አቀፍ ተደማጭነት የሚያጎላ እንደሆነ አሜሪካ ታምናለች።

ትራምፕ ከኬንያ ጋር በቀጥታ ከተስማሙ በኋላ ተመሳሳይ መንገድ ተጠቅመው ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች ጋር የመሥራት ውጥን እንዳላቸው ሙር ይናገራሉ።

ይህ የትራምፕ መንገድ፤ ከአፍሪካ ሕብረት የንድግና ኢንዱስትሪ ኮሚሽነር አልበርት ሙቻንጋን ሐሳብ ጋር ይጣረሳል።

እሳቸው የአፍሪካ አገራት በተናጠል ሳይሆን በአንድነት ከአሜሪካ ጋር ስምምነት እንዲያደርጉ ይፈልጋሉ።

ሙር እንደሚሉት፤ የአሜሪካ ውሳኔ የአፍሪካ ሕብረት የአህጉሪቱን ምጣኔ ሀብት ለማጣመር ከሚያደርገው ጥረት ጋር ይጣረሳል።

ሕብረቱ፤ አፍሪካን የዓለም ትልቋ ነጻ የንግድ ቀጠና የማድረግ አላማ አለው።

ትራምፕ ግን በጥምረት ከሚሠሩ ኃይሎች ጋር በጋራ ያለመደራደር አዝማሚያ ያሳያሉ ሲሉ አጥኚው ያክላሉ።

የትራምፕ ተቀናቃኝ ጆ ባይደን ካሸነፉ የአፍሪካ ፖሊሲያቸው ምን እንደሚሆን እስካሁን አልገለጹም።

"የባይደን አስተዳደር በኦባማ ጊዜ ወደነበረው ሂደት ሊመለስ ይችላል" ይላሉ ሙር።