ክለባቸውን ሊለቁ የሚችሉ ዘጠኝ የፕሪምየር ሊጉ ተጫዋቾች

የዘንድሮው የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት የፊታችን ሃሙስ በይፋ ይዘጋል። ብዙ የእንግሊዝ ክለቦች የመጨረሻው ቀን ከመድረሱ በፊት ይጠቅሙኛል ያሏቸውን ተጨዋቾችን ለማስፈረም እየተሯሯጡ ነው።

ቶተንሃም በመጨረሻም ተጫዋች ያስፈርም ይሆን? የማንቸስተሩ አንቶኒ ማርሻል ወደ ሌላ ክለብ ይዘዋወር ይሆን?

በዚህኛው የዝውውር መስኮት ክለቦቻቸውን ሊለቁ የሚችሉ ዘጠኝ የፕሪምየር ሊጉ ተጫዋቾችን እንመልከት።

ቶቢ አልደርዌረልድ (ቶተንሃም)

ቶቢ አልደርዌረልድ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ቤልጂየማዊው ተከላካይ ባለፈው ዓመት ባጋጠመው ጉዳት ምክንያት በቶተንሃም የቋሚ አሰላለፍ ቦታ ለማግኘት ተቸግሮ ነበር። ኮንትራቱ በዚህ ዓመት የሚጠናቀቀው አልደርዌረልድ፤ ስሙ ከማንቸስተር ዩናይትድ ጋር እየተያያዘ ነው። ለተጫዋቹ የቀረበው የመግዣ ዋጋ ደግሞ 75 ሚሊዮን ፓውንድ ነው።

ጃክ ግሬሊሽ (አስቶን ቪላ)

ጃክ ግሬሊሽ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የ21 ዓመቱ እንግሊዛዊ ግሬሊሽ በቻምፒዮንሺፑ አስቶን ቪላ ላደረገው ግስጋሴ ከፍተኛ አስተዋጸኦ አድርጓል። ክለቡ በአሁኑ ሰአት የገንዘብ እጥረት ያጋጠመው ሲሆን፤ በተለይ ደግሞ ቶተንሃሞች ተጫዋቹን የግላቸው ለማድረግ እስከ 20 ሚሊዮን ፓውንድ ለመክፈል ተዘጋጅተዋል። አስቶን ቪላ ግን ቶተንሃሞች ያቀረቡትን ዋጋ እጥፍ እየጠየቁ ነው።

ዳኒ ኢንግስ (ሊቨርፑል)

ዳኒ ኢንግስ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

በአንድ ወቅት እንግሊዝ ካፈራቻቸው ምርጥ አጥቂዎች መካከል አንዱ ተብሎ ሲወደስ ነበረው ዳኒ ኢንግስ ሊቨርፑል ባሳለፋቸው ሶስት ዓመታት እጅግ አስቸጋሪ ጊዜ አሳልፏል። በባለፈው የእንግሊዝ ፕሪምየር ሊግም አንድ ጊዜ ብቻ ነው ግብ ማስቆጠር የቻለው።

ሊቨርፑሎችም ለተጫዋቹ የ20 ሚሊዮን ፓውንድ መሸጫ ዋጋ ለጥፈውበታል። ተጫዋቹን በጥብቅ ከሚፈልጉት ክለቦች መካከል ደግሞ ክሪስታል ፓላስ የመጀመሪያውን ስፍራ ይዟል።

ሃሪ መጓየር (ሌስተር ሲቲ)

ሃሪ መጓየር

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

በተለይ በአለም ዋንጫው ለእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ያሳየው ወጥና አስገራሚ አቋም በአሁኑ ሰአት ይህን ተከላካይ ተፈላጊ እንዲሆን አድርጎታል።

የሃሪ መጓየር ዋነኛ ፈላጊ ደግሞ የማንቸስተር ዩናይትዱ አሰልጣኝ ሆሴ ሞሪንሆ ናቸው። ለተጫዋቹም እስከ 56 ሚሊዮን ፓውንድ ለመክፈል ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል። የተጫዋቹ ባለቤት ሌስተር ሲቲ ደግሞ ለተከላካዮች ሪከርድ የሆነ 80 ሚሊዮን ፓውንድ ጠይቀዋል።

አንቶኒ ማርሻል (ማንቸስተር ዩናይትድ)

አንቶኒ ማርሻል

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ከአሌክሲስ ሳንቼዝ ወደ ማንቸስተር ዩናይትድ መምጣት በኋላ አንቶኒ ማርሻል የቋሚ አሰላፍ ቦታ ለማግነት ተቸግሮ የቆየ ሲሆን፤ ለአለም ዋንጫው በብሄራዊ ቡድኑ አለመካተቱ ደግሞ ክለቡን እንዲለቅ ምክንያት ሊሆነው እንደሚችል ተገልጿል።

በሌላ በኩል ተጫዋቹ ሁለተኛ ልጅ ሲወለድለት የቅድመ ውድድር ጨዋታውን ጥሎ ወደ ፈረንሳይ መመለሱ የማንቸስተሩ አሰልጣን ሆዜ ሞሪንሆን ያስደሰታቸው አይመስልም። መሸጫ ዋጋውም እስከ 80 ሚሊዮን ፓውንድ ይደርሳል ተብሏል።

ሲሞን ሚኞሌ (ሊቨርፑል)

ሲሞን ሚኞሌ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ቤልጂየማዊው ግብ ጠባቂ በሊቨርፑል ቤት የቋሚ አሰላለፍ ቦታውን በካሪየስ ተነጥቆ ነው የቆየው። አሁን ደግሞ ብራዚላዊውን ግብ ጠባቂ አሊሰን ከሮማ ማስፈረማቸው ደግሞ የተጠባባቂውን ቦታ እንኳን እንዳያገኝ ሊያደርገው ይችላል።

በአስገራሚ ሁኔታ የላሊጋው አሸናፊ ባርሴሎናዎች በግብ ጠባቂው ላይ ፍላጎት አሳይተዋል።

አሮን ራምሴ (አርሰናል)

አሮን ራምሴ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ዌልሳዊው አማካይ ራምሴ በአርሰናል ቤት 10 ዓመት የቆየ ሲሆን፤ 300 ጨዋታዎችን ደግሞ ለክለቡ አድርጓል። አዲሱ የአርሰናል አሰልጣኝ ኡናይ ኤምሪ ራምሴን ጠቃሚ ተጫዋች ነው ብለው ቢገልጹትም፤ ከቼልሲ የቀረበላቸው የ35 ሚሊዮን ፓውንድ መገዣ ዋጋ እና የሊቨርፑል ፍላጎት ሃሳባቸውን ሊያስቀይራቸው እንደሚችል ይገመታል።

ዊሊያን (ቼልሲ)

ዊሊያን

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ይህ የማይደክመው የሚባልለት የክንፍ ተጫዋች በአለም ዋንጫው ለሃገሩ ብራዚል በአምስቱም ጨዋታዎች በቋሚ አሰላለፍ ውስጥ መግባት ችሏል። ባለፈው ዓመት ቼልሲ በኤፍ ኤ ካፕ የፍጻሜ ጨዋታ ከማንቸስተር ይናይትድ ጋር ሲጫወቱ በቀድሞው አሰላጣኝ አንቶኒዮ ኮንቴ ተጠባባቂ ቦታ ላይ መቀመጡ ደግሞ ልቡን እንዳስሸፈተው ይገመታል።

የተጫዋቹ ዋነኛ ፈላጊ ሆነው እየተፎካከሩ ያሉት ደግሞ ሪያል ማድሪድ፤ ባርሴሎና እና ማንቸስተር ዩናይትድ ሲሆኑ፤ 65 ሚሊዮን እንዲፍሉ ተጠይቀዋል።

ዊልፍሬድ ዛሃ (ክሪስታል ፓላስ)

ዊልፍሬድ ዛሃ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ምንም እንኳን የባለፈው ዓመት የውድድር ዘመን የመጀመሪያዎቹን ስድስት ጨዋታዎች ለቡድኑ መሰለፍ ባይችልም፤ ከዚያ በኋላ ባደረጋቸው ጨዋታዎች ግን ዘጠኝ ግቦችን አስቆጥሮ ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን ለቡድን አጋሮቹ አመቻችቶ አቀብሏል።

አሰልጣኝ ሮይ ሆድሰን ኮትዲቯራዊውን ተጫዋች በቡድናቸው ለማስቀረት ጥረት እያደረጉ ቢሆንም፤ ከተለያዩ ክለቦች እየቀረበላቸው ያለው ከፍተኛ ገንዘብ ሃሳባቸውን ሊያስቀይራቸው እንደሚችል ይገመታል።