'በተለያዩ የኦሮሚያ ዞኖች ከዓለም ዓይን የተሰወረ ጦርነት እየተካሄደ ይገኛል' ኦፌኮ

የኦፌኮ መግለጫ

በተለያዩ የኦሮሚያ ዞኖች ከዓለም ዓይን የተሰወረ ጦርነት እየተካሄደ የሰው ህይወት እየጠፋ ነው ሲል የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ዛሬ ግንቦት 04/2014 ዓ.ም. አዲስ አበባ ውስጥ በሰጠው መግለጫ አመለከተ።

ፓርቲው እየተካሄደ ነው ባለው ጦርነት በርካታ ዜጎች በጅምላ መገደላቸውን ገልጾ፣ እየተፈጸሙ ያሉት የጅምላ ግድያዎች ገለልተኛ በሆነ ዓለም አቀፍ አካል እንዲጣራም ጠይቋል።

"አሁን ይህን መግለጫ በምንሰጥበት ጊዜ ከተቀረው ዓለም ዓይን የተሰወረ ጦርነት በኦሮሚያ ክልል እየተካሄደ ነው" ሲል ከዋነኞቹ የኦሮሞ የፖለቲካ ቡድኖች መካከል አንዱ የሆነው ኦፌኮ ገልጿል።

ባለፉት ጥቂት ወራት ብቻ ፓርቲው ንጹሃን ናቸው ያላቸው ከ297 በላይ ሰዎች በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በመንግሥት ኃይሎች ተገድለዋል ያለ ሲሆን፤ ግጭቶችን ተከትሎም ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ሰዎች ቀያቸውን ጥለው ለመሰደድ ተገደዋል ብሏል።

"ከፍርድ ቤት ትዕዛዝ ውጪ የሚታሰሩ አሉ። ሰዎች ከፍርድ ውጪ እየተገደሉ ነው። ታፍነው የሚወሰዱ ሰዎች አሉ" ብሏል የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ በሰጠው መግለጫ።

በኦሮሚያ እና በሌሎች ክልሎች በዜጎች ላይ የጅምላ ግድያ የሚፈጽሙ አካላት ለፍርድ እንዲቀርቡ ጠይቋል።

ፓርቲው በመግለጫው የአገሪቱ የፍርሕ ሥርዓት መዳከሙን እና የመንግሥት ባለሥልጣናት የፍርድ ቤቶችን ትዕዛዝ እንደማያከብሩ ጨምሮ ገልጿል።

አገሪቱ ጦርነት ውስጥ በመግባቷ ከፍተኛ የምጣኔ ሀብት ውድቀት መከሰቱን የገለጸው ኦፌኮ፤ "ጦርነቱ መፍትሄ ካላገኘ የፖለቲካ ቀውስ እና የምጣኔ ሀብት ችግሩ አገሪቱን ወደ ውስብበስ ሁኔታ ይዞ መግባቱ የማይቀር ነው" ሲል አስጠንቅቋል።

ለዚህም ጦርነት ቆሞ ላሉ ችግሮች ፖለቲካዊ መፍትሄ መሰጠት አለበት ብሏል።

ፋኖ እና ሌሎች የአማራ ክልል ኃይሎች

የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ በመግለጫው እየተፈጸሙ ናቸው ላላቸው ግድያዎች የአማራ ክልል ኃይሎችን ተጠያቂ አድርጓል።

ፓርቲው ፋኖ፣ የአማራ ሚሊሻ እና የአማራ ልዩ ኃይል በክልሉ መንግሥት ተደግፈው በአማራ ክልል፣ በኦሮሚያ እና በቤኒሻንጉል ክልሎች "ንጹሃን ዜጎችን እየገደሉ ነው" ሲል ከሷል።

እነዚህ ኃይሎች ከግድያ በተጨማሪ ከብት እና እህል ይዘርፋሉ፣ እንዲሁም ቤቶችን ያቃጥላሉ ብሏል በመግለጫው።

ፓርቲ ጨምሮም በአማራ ክልል ታጣቂዎች ለክልሉ እና ለአገሪቱ ስጋት በሚሆን መልኩ ታጥቀው በመደራጀት አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሰዋል ብሏል።

ብሔራዊ ምክክር

ኦፌኮ በአገሪቱ ለመካሄድ ዝግጅት እየተደረገበት ስላለው ብሔራዊ ምክክርን በተመለከተም "በስመ ብሔራዊ ምክክር እየተካሄደ ያለው እንቅስቃሴ ቀልድ ከመሆኑ ባለፈ፤ ያሉትን ችግሮች የበለጠ የሚያወሳስብ፣ አደጋን የሚያስከትል አካሄድ ነው" ብሎታል።

ጨምሮም በአገሪቱ ብሔራዊ ምክክርን ለማካሄድ የተዋቀረው ኮሚሽንም ሆነ አካሄዱ ነጻ እና አሳታፊ አይደለም በማለት ኦፌኮ ያለውን አቋም ገልጿል።