ፕሬዝደንት ማክሮንን በጥፊ የተማታው ግለሰብ እስር ተፈረደበት

የፎቶው ባለመብት, EPA
የፈረንሳዩን ፕሬዝደንት ኢማኑኤል ማክሮን በሥራ ጉብኝት ላይ እያሉ በጥፊ የተማታው ግለሰብ የአስራ ስምንት ወራት እስር ተፈረደበት።
ከትናንት በስቲያ ማከሰኞ ዕለት ፕሬዝደንት ማክሮን በይፋዊ የሥራ ጉብኝት ላይ ሰላምታ እየተሰጧቸው የነበሩ ሰዎችን እየጨበጡ ሳለ ነበር በአንድ ግለሰብ በጥፊ የተመቱት።
ፕሬዝደንቱ በጥፊ ሲመቱ የሚያሳየው ተንቀሳቃሽ ምስል ማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ በስፋት ተሰራጭቷል።
ዳሚኤን ታሬል የተባለው ግለሰብ ፕሬዝደንቱን መማታቱን ለፍርድ ቤት በሰጠው ቃል አምኗል። ዐቃቤ ሕግ ግለሰቡ ሆነ ብሎ የኃይል እርምጃ ወስዶ ፕሬዝደንቱን ተማትቷል ሲል ከሶታል።
በጥፊ የተማታው ግለሰብ "ማክሮኒዝም ይውደም" እያለ ነው ፕሬዝዳንቱን በጥፊ የመታቸው።
ማክሮን በጥፊ ከተመቱ በኋላ በድጋሚ ወደ ስፍራው ተመልሰው ከማኅበረሰቡ ጋር ሲነጋገሩ በተንቀሳቃሽ ምስሉ ታይቷል።
የግለሰቡ ድርጊት በመላው ፈረንሳይ በርካቶችን ያስቆጣ ነበር። ዐቃቤ ሕግም ግለሰቡ በ18 ወራት እስር እንዲቀጣ ጠይቆ ነበር።
ፍርድ ቤቱ ግለሰቡ ላይ የ18 ወራት እስር ቢፈርድበትም 14ቱ በይርጋ የሚታይ ይሆናል ብሏል።
ማክሮንን በጥፊ በመማታት ጥፋተኛ የተባለው ግለሰብ የ4 ወራት እስሩን የሚጀምር ሲሆን በቀጣዮቹ 18 ወራት ውስጥ ጥፋት አጥፍቶ ቢገኝ የ18 ወራት ፍርዱ የጸና ይሆናል።
ማክሮንን የተማታው ዳሚኤን ታሬል ፕሬዝደንቱን ለምን እንደተማታ ሲጠየቅ፤ ከጓደኛው ጋር የፕሬዝደንቱን ጉብኝት መኪናቸው ውስጥ ሆነው እየጠበቁ ሳለ በሁሉም ዘንድ የሚወሳ ተግባር ለመፈጸም ማቀዱን ተናግሯል።
ግለሰቡ ኃይል የመጠቀም ሃሳብ አልነበረኝም ብሏል።
ፕሬዝደንቱ ላይ እንቁላል ወይም ክሬም ኬክ ለመወርወር አቅዶ የነበረ ቢሆንም ፕሬዝደንቱ ቀርበውት "ድምጼን [የምርጫ] ልሰጠው እንደምችል ሲገምተኝ በጣም ተበሳጨሁ" በማለት ስለመናገሩ ተዘግቧል።












