ፈረንሳይ ሀብታም አገራት ካከማቹት ክትባት 5 ከመቶውን ለድሀ አገሮች እንዲሰጡ ጠየቀች

የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን

የፎቶው ባለመብት, EPA

የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን አውሮጳና አሜሪካ በአስቸኴይ የክትባት ክምችታቸውን 5 እጅ ለድሀ አገራት እንዲሰጡ ሐሳብ አቀረቡ።

ማክሮን ለፋይናንሻል ታይምስ ጋዜጣ እንደተናገሩት በክትባቱ ዙርያ ፍትሐዊ አለመሆን አለመመጣጠንን ይፈጥራል።

እስከአሁን ሙሉ በሙሉ ማለት በሚቻል ሁኔታ ክትባት እየተሰጠ ያለው ለሀብታም አገራት ነው።

ማክሮን ይህን ያለተመጣጠነ ዓለም አቀፍ የክትባት ሥርጭትን ለማመጣጠን ይህን ሐሳብ ያቀረቡት ጂ 7 በመባል የሚታወቁት ብልጹግ አገራት ስብሰባ አርብ ከመደረጉ ቀደም ብለው ነው።

ዋይት ሐውስ እንዳስታወቀው ጆ ባይደን የ4 ቢሊዮን ዶላር ለኮቫክስ ፕሮጀክት ይለግሳሉ ብሏል። ኮቫክስ የሚባለው ፕሮጀክት ክትባትን ለድሀ አገሮች ለማድረስ የሚሰራ ጥምረት ነው።

የታላቋ ብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትርና የስብሰባው የወቅቱ ሊቀመንበር ቦሪስ ጆንሰን በበኩላቸው በርከት ያለ ክትባት ለኮፋክስ እንደሚለግሱ እየተጠበቀ ነው።

እንደ ጆን ሆፕኪንስ መረጃ ከሆነ እስከአሁን 110 ሚሊዮን ሕዝብ በተህዋሲው የተያዘ ሲሆን 2ሚሊዮን 400ሺህ የሚሆን ሕዝብ ሞቷል።

ባለፈው ረቡዕ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒኦ ጉተሬዝ ያልተመጣጠነና ፍትሐዊ ያልሆነውን የክትባት ሥርጭት መተቸታቸው ይታወሳል።

እሳቸው እንዳሉት 10 ብልጹግ አገሮች የጠቅላላው ክትባት 75 ከመቶ ለብቻቸው ይዘውታል። 130 አገሮች ግን አንድም ክትባት ጠብታ ለዜጎቻቸው አልሰጡም።

ሃብታሞቹ አገራት ክትባቱን ከሚያስፈልጋቸው ቁጥር በላይ ይዘው እያከማቹ መሆኑም ሌላው አነጋጋሪ ጉዳይ ነው።

ለምሳሌ ታላቋ ብሪታኒያና ካናዳ ያዘዙት የክትባት ብዛት መላ ሕዝባቸው ክትባቱን ደግሜ ለውሰድ ቢል ራሱ በቅቶ የሚተርፍ ነው።

የጤና ባለሙያዎች ፍትሐዊ የኮቪድ ክትባት በዓለማችን ከሌለ ወረርሽኙን መቆጣጠር አዳጋች ይሆናል ብለው ያምናሉ።

ከነገ በስቲያ አርብ ብልጹጎቹ የጂ 7 አባል አገር መሪዎች ይህን ኢፍትሐዊ የክትባት ሥርጭት እንዴት ፍትሐዊ እናድርግ በሚለው ላይ አንድ ስምምነት ይደርሳሉ ተብሎ እየተጠበቀ ነው።