ጋዜጠኛ፡ ኬንያዊውንና የኦኤምኤን ጋዜጠኛን ጨምሮ 9 ሰዎች በዋስ እንዲፈቱ ተወሰነ

ኬንያዊው ጋዜጠኛ ያሲን ጁማ፣ የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ጋዜጠኛ መለሰ ዲሪብሳን ጨምሮ ዘጠኝ ሰዎች በዋስ እንዲፈቱ ፍርድ ቤት ወሰነ።
የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት በጪብሳ አብዱልከሪም መዝገብ ውስጥ የተከሰሱ ሰዎች የዋስ መብታቸው ተከብሮ እንዲፈቱ በዛሬው ዕለት ትዕዛዝ አስተላልፏል።
ተጠቀሰው መዝገብ ውስጥ አምስት ተከሳሾች የሚገኙ ሲሆን፣ እነዚህም የኦኤምኤን ጋዜጠኛ መለሰ ዲሪብሳ፣ ኬንያዊው ጋዜጠኛ ያሲን ጁማ፣ ሃሰን ጂማ እና ፈይሳ ባሳ ናቸው።
ግለሰቦቹ በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉት የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ አስከሬን በኃይል ወደ አዲስ አበባ እንዲመለስና እንዲጉላላ በማድረግ እንዲሁም በተለያዩ ብሄሮችና ሃይማኖቶች መካከል ግጭት እንዲቀሰቀስ አድርገዋል በሚል ተጠርጥረው ነው።
አርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ መገደሉን ተከትሎ ከፍተኛ የፖለቲካ አመራሮች፣ ጋዜጠኞችና ነዋሪዎችን ጨምሮ ከ7ሺህ በላይ ሰዎች በአዲስ አበባና በኦሮሚያ ክልል በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ማስታወቃቸው የሚታወስ ነው።
ለቢቢሲ አስተያየታቸውን የሰጡት የተከሳሾች ጠበቃ አቶ ከዲር ቡሎ፤ ደንበኞቻቸው ፈጽመውታል የተባለው ወንጀል በማስረጃ መቅረብ ባለመቻሉ በ3ሺህ ብር ዋስትና እንዲፈቱ ፍርድ ቤቱ መወሰኑን ተናግረዋል።
ከዚህ በተጨማሪም በአቶ ጆምባ ሁሴን የክስ መዝገብ ላይ ኢብራሂም አብዱልጀሊል፣ ኪያር፣ መሐመድ፣ ኦብሳ እና አለማየሁ የሚባሉ ግለሰቦችም በ4ሺህ ብር ዋስ ከእስር እንዲወጡ ፍርድ ቤቱ ማዘዙን ጠበቃው አቶ ከድር ለቢቢሲ ተናግረዋል።
ፍርድ ቤት ተጠርጣሪዎቹን "የዋስትና መብታቸው ተጠብቆ፣ ከእስር ይውጡ ብሎ እስካዘዘ ድረስ ፖሊስ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ ሊለቃቸው ይገባል" ብለዋል አቶ ከድር።
"የቤተሰብ አባላት ለዋስትና የተጠየቀውን ብሩን ለመክፈል እየተሯሯጡ ይገኛሉ። ፖሊስ የፍርድ ቤት ትዕዛዝን አክብሮ ሊለቃቸው ይገባል" በማለትም በተጨማሪ ለቢቢሲ አስረድተዋል።












