የዛምቢያ ፍርድ ቤት ከካናቢስ እፅ ኬክ የጋገረውን ተማሪ 'ደብዳቤ ፃፍ' በማለት ቀጣ

የፎቶው ባለመብት, Drug Enforcement Commission
የዛምቢያ ፍርድ ቤት ከካናቢስ እፅ የተጋገሩ ኬኮችን ለመሸጥ እቅድ በነበረው የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ላይ ዘለግ ያለ ደብዳቤ እንዲፅፍ ቅጣት አስተላልፏል።
በኮፐርቤልት ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዓመት የምህንድስና ተማሪ የሆነው ቸሂክዋንዳ ቺሴንደሌ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር የዋለ ሲሆን 1 ኪሎግራም የሚመዝንና በካናቢስ እፅ የተቀባ ኬክ ይዞ መገኘቱን ፖሊስ አስታውቋል።
ፍርድ ቤቱ በ21 ዓመቱ ተማሪ ላይ ከጣለው ቅጣት በተጨማሪ ለጥፋቱ በእፅ አጠቃቀም ዙሪያ 50 ገጽ ሃተታ እንዲፅፍ ፍርድ ቤቱ በይኖበታል።
ፍርድ ቤቱ አክሎም ተማሪው ለዩኒቨርሲቲው፣ ለቤተሰቦችን እና ለዛምቢያ የእፅ ቁጥጥር ኮሚሽን ከሕዳር 15 በፊት የይቅርታ ደብዳቤ እንዲፅፍ አዞታል።
ከዚህም ባሻገር ተማሪ ቺሴምቤል በሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ከምንም ዓይነት ወንጀል ራሱን እንዲያቅብ ካልሆነ ግን ለእስር እንደሚዳረግ ውሳኔ ተላልፎበታል።

የእፅ ቁጥጥር ኮሚሽኑም "ሰዎችን በእፅ ለማደንዘዝ የካናቢስ ኬክ በመጋገር ያልተገባ ጥረት አድርጓል" ሲል ተማሪውን ኮንኖታል።
ኮሚሽኑ ለዩኒቨርሲቲዎች ባስተላለፈው ማሳሰቢያ "በካናቢስና በሌሎች እፆች የተጋገሩ ኬኮች በተማሪዎች ዘንድ እየተዘዋወሩ ስለመሆን አለመሆኑ ዐይናቸውን ከፍተው በጥንቃቄ መከታታል አለባቸው" ብሏል።
በዛምቢያ ሕግ መሠረት ማሪዋና ከአደገኛ እፆች ተርታ የሚመደብ ሲሆን እፁን ይዞ መገኘት በጥብቅ የተከለከለ ነው።
በመሆኑም እንደ ካናቢስ ያሉ እፆችን ማዘዋወር፣ መጠቀም እና ይዞ መገኘት የገንዘብ ቅጣት አሊያም እስር ሊያስከትል ይችላል።
ዛምቢያ፤ በተለይ በካናቢስ እና ሄሮይን እፅ አጠቃቀምና ዝውውር ስትፈተን ቆይታለች።















