ትራምፕ የሕንዱን ጠቅላይ ሚኒስትር አሞካሹ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ እና የሕንዱ ጠቅላይ ሚንስትር ናሬንድራ ሞዲ በቴክሳስ ግዛት ሂውሰትን ከተማ በተዘጋጀ መደረክ ላይ ሲሞጋገሱ አምሽተዋል።
"ዛሬ እዚህ በቴክስሳ ከአሜሪካ ቁልፍ አጋር፣ ታታሪ እና ታማኝ ወደጅ ከሆኑት ከጠቅላይ ሚንስትር ናሬንድራ ሞዲ ጋር በመገኘቴ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶኛል" በማለት ለ50ሺህ ታዳሚዎች የተናገሩት ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ናቸው።
ጠቅላይ ሚንስትር ሞዲ በበኩላቸው፤ ፕሬዝደንት ትራምፕን በዋኃይት ሃውስ የሚገኝ "እውነተኛ ጓደኛ" ብለው ከገለጹ በኋላ፤ "ከዋና ሥራ አስፈጻሚ ወደ የአሜሪካ ጦር ጠቅላይ አዛዥ፣ ከቦርድ ስብሰባ አዳራሽ ወደ ዋኃይት ሃውስ፣ . . . ትራምፕ በየሄዱበት አሻራቸውን ጥለው የሚያልፉ መሪ" ሲሉ አሞካሽተዋቸዋል።
ትራምፕ "እጅግ አስደናቂ እና ታሪካዊ ክስተት'' ሲሉ በገለጹት መድረክ ከ50ሺህ በላይ ሰዎች ተሳታፊ ሆነውበታል።
ለ 90 ደቂቃ የቆየው ዝግጅት በአሜሪካ ታሪከ ለውጪ ሃገር መሪ ከተሰናዱ ደማቅ አቀባበሎች መካከል አንዱ ነው ተብሎለታል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ይህ መድረክ በ 2020 ለሚካሄደው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ትራምፕ ትውልደ ሕንድ የሆኑ አሜሪካውያንን ድጋፍ ለማገኘት እንደሚረዳቸው ታምኗል። ለጠቅላይ ሚንስትር ሞዲ ከትራምፕ የተቸራቸው ውዳሴ በሕንድ እየቀረበባቸው ያለውን የሰላ ትችት ያለዝበዋል ተብሏል።
ትራምፕ በስታዲየሙ ተሰብሰበው ለነበሩት ትውልደ ሕንድ አሜሪካውያን ታዳሚዎች "አሜሪካዊ ሆናችሁ ከእኛ ጋር ስለሆናችሁ ኩራት ይሰማናል" ብለዋል።
የሕንዱ ጠቅላይ ሚንሰትር አንድ ሳምንት በሚቆየው የአሜሪካ ጉብኝታቸው ከአሜሪካ ጋር በንግድ ላይ ያተኮረ ውይይት እንደሚያደርጉ የሚጠበቅ ሲሆን በተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ስብሰባ ላይም ተሳታፊ ይሆናሉ።












