የሜክሲኮ ፕሬዝዳንት አውሮፕላናቸውን ሸጠው ሕገ-ወጥ ስደትን ሊቀንሱ አስበዋል

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የሜክሲኮው ፕሬዝዳንት አንድሬ ማኑዌል ሎፔዝ ኦብራዶር አውሮፕላናቸውን ሸጠው የሚያገኙትን ትርፍ ሕገ-ወጥ ስደትን ሊከላከሉበት እንደሆነ አሳውቀዋል።
ፕሬዝዳንቱ ሃሳቡን ያመጡት ሃገራቸው ሜክሲኮ ከአሜሪካ ጋር በደረሱት ስምምነት መሠረት ሲሆን ስምምነቱ ሜክሲኮ ከማዕከላዊ ወደ አሜሪካ የሚደረገውን ጉዞ መግታት የምትችል ከሆነ የዶናልድ ትራምፕ መንግሥት ሜክሲኮ ላይ የጫነውን ቀረጥ እንደሚቀንስ ያትታል።
ፕሬዝዳንቱ በምረጡኝ ቅስቀሳቸው ወቅት የፕሬዝዳንቱን አውሮፕላን ሸጬ ደሃ ሜክሲኳዊያንን ሕዝብ እረዳለሁ ሲሉ ቃል ገብተው ነበር።
ቦይንግ 787 ድሪምላይነር የተሰኘው የፕሬዝዳንቱ አውሮፕላን 150 ሚሊዮን ዶላር [ከ4 ቢሊዮን ብር በላይ ገደማ] ያወጣል ተብሎ ይጠበቃል።
ስማቸው የረዘመባቸው የሃገሪቱ ሰዎች 'አምሎ' ብለው የሚጠሯቸው ፕሬዝዳንት ሎፔዝ አውሮፕላኑን ሸጨ እኔ ከሕዝብ ጋር ተጋፍቼ እሄዳለሁ ሲሉ ነበር ቃል የገቡት።
አውሮፕላኑ ላለፉት ጥቂት ወራት ካሊፎርኒያ የሚገኝ አንድ መጋዘን ውስጥ ለሻጮች ክፍት ሆኖ ቆይቷል።
ሜክሲኮ የፕሬዝዳንቱን አውሮፕላን አክሎ ሌሎች 60 የመንግሥት አውሮፕላኖችንና 70 ሄሊኮፕተሮችን ለመሸጥ ቆርጣ ተነስታለች።
ሜክሲኮ ሶስተኛዋ ሃያል የአሜሪካ የንግድ አጋር ስትሆን ከዶናልድ ትራምፕ ጋር በነበራት እሰጥ-አገባ ምክንያት ከሜክሲኮ የሚመጡ ምርቶች ላይ ቀረጥ ተጭኖ ነበር።
ሜክሲኮ አውሮፕላኗን ከመሸጥ አልፋ 6 ሺህ ገደማ ፖሊሶችን ወደ ጓቲማላ ልካ ሕገ-ወጥ ስድትን ለመግታት ቃል ገብታለች።
የፕሬዝዳንቱ አውሮፕላን መሸጥ ለበርካታ ሜክሲኳውያን የተዋጠ አይመስልም፤ በሕዝብ ገንዘብ የተገዛ ንብረትን እንዴት ተደርጎ? እያሉም ይገኛሉ።












