በሱዳን በተቀሰቀሰ ግጭት ቢያንስ ሰባት ሰዎች ሞቱ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በሱዳን፣ ካርቱም በተፈጠረ ግጭት የፀጥታ ኃይልን ጨምሮ በትንሹ ስድስት ሱዳናውያን ተቃዋሚዎች መሞታቸው ተሰምቷል።
ሰልፈኞቹ በወታደራዊ ዋና መሥሪያ ቤት አካባቢ ተሰባስበው የሲቪል መንግሥት እንዲመሰረት በሚጠይቁበት ወቅት በተተኮሰ ጥይት ተገድለዋል ተብሏል።
ተቃዋሚዎች ተኩሱን የከፈቱት ወታደሮች ናቸው ቢሉም፤ ወታደሮቹ ግን ተኳሾቹ ማንነታቸው ያልታወቀ አካላት እንደሆኑ ተናግረዋል።
ባለፈው ወር ፕሬዚደንት ኦማር አል በሽር ከሥልጣን መውረዳቸውን ተከትሎ፤ ሱዳን በሽግግር ወታደራዊ ምክር ቤት እየተዳደረች ትገኛለች።
ፕሬዚደንቱ ከሥልጣን ከመውረዳቸው ከስድስት ቀናት አስቀድሞም ተቃዋሚዎች በዋናው ወታደራዊ መሥሪያ ቤት አቅራቢያ ያለውን አደባባይ ተቆጣጥረውት እንደነበር ይታወሳል።
የወታደራዊ መንግሥቱና የተቃዋሚዎች ስምምነት
ሰኞ ዕለት የተቃዋሚዎች ጥምረትና ሀገሪቷን እየመራ ያለው ወታደራዊ መንግሥት በሽግግሩ ወቅት ስለሚኖረው የሥልጣን ተዋረድ ስምምነት ላይ ደርሰዋል።
የተቃውሞ እንቅስቃሴው ቃል አቀባይ ታሃ ኦስማን "በዛሬው ስብሰባችን የሥልጣን ተዋረዱና ክፍፍሉ ላይ ስምምነት ላይ ደርሰናል" ሲሉ ለኤ ኤፍ ፒ የዜና ወኪል ገልፀዋል።
ቃል አቀባዩ የስልጣን ተዋረዱ የከፍተኛው ምክር ቤት፣ የካቢኔት ምክር ቤት እና የሕግ አውጭው አካል እንደሆነ ዘርዝረዋል።
ወታደራዊ ምክር ቤቱ በበኩሉ በሽግግር መንግሥቱ የሥልጣን ተዋረድ ላይ ሥምምነት ላይ መድረሱን አስታውቋል።
ሁለቱ አካላት ዛሬ በሚኖራቸው ስብሰባ የሽግግር መንግሥቱ ለምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይና በሥልጣን መዋቅሩ የሚካተቱ አካላት ኃላፊነት ላይ ስምምነት እንደሚደርሱ ይጠበቃል።
ጄኔራሎቹ የሽግግሩ ወቅት ሁለት ዓመት መሆን አለበት ቢሉም ተቃዋሚዎች አራት ዓመታት እንዲሆን ይፈልጋሉ።












