የሱዳን ተቃዋሚ ሰልፈኞች ወታደሩ ያስቀመጠውን ሰዓት እላፊ ጣሱ

የፎቶው ባለመብት, EPA
በትናንትናው ዕለት ሱዳንን ለሰላሳ ዓመታት ያስተዳድሩት አል በሽር በወታደሩ ከስልጣን መውረዳቸውን ተከትሎ የተጣለውን የሰዓት እላፊን በመተላለፍ ሱዳናውያን ምሽቱን ጎዳና ላይ አሳልፈዋል።
ለረዥም ወራት ተቃውሞ ሲቀርብባቸው የነበሩት የቀድሞው የሱዳን ፕሬዝዳንት ከስልጣን ተነስተው በቁጥጥር ስር የዋሉት ትናንት ሐሙስ ዕለት ነበር።
ተቃዋሚ ሰልፈኞች ግን የወታደሩ ምክር ቤት የአል በሽር አስተዳደር ውስጥ የነበረ ነው ሲሉ ተቃውመዋል።
እንደ አዲስ ያገረሸው ተቃውሞ በወታደሩ እና በተቃዋሚ ሰልፈኞቹ መካከል ግጭት እንዳያስነሳ ተሰግቷል።
በተጨማሪም የተለያዩ የደህንነት ኃይሎችና ሚሊሻዎች እርስ በእርሳቸው ጦር እንዳይማዘዙ ስጋት አለ።
የተባበሩት መንግሥታትም ሆነ የአፍሪካ ሕብረት በሀገሪቱ መረጋጋት እንዲሰፍን ጥሪ አቅርበዋል።
የ75 አመቱ አል በሽር ከስልጣን የመውረዳቸውን ዜና ተከትሎ የነበረው የደስታ እና የፈንጠዚያ ስሜት የተቃውሞ ሰልፉ አስተባባሪዎች በጦር ሠራዊቱ ዋና መስሪያ ቤት ደጃፍ የመቀመጥ አድማው እንዲቀጥል መናገራቸወን ተከትሎ ተቀዛቅዟል።
"ይህ የቀደመው ሥርዓት ቅጣይ ነው" ብላለች ሳራ አብደልጃሊል የሱዳናውያን ባለሙያዎች ማህበር አባል " ስለዚህ በሰላማዊ ተቃውሟችን መግፋትና መታገል አለብን።"
ትናንትና በሀገሪቱ ቴሌቪዥን በተነበበው መግለጫ ላይ ከምሽቱ አራት ሰዓት እስከ 10 ሰዓት ድረስ ሰዓት እላፊ መታወጁ ተገልጦ ነበር።
በመግለጫው "ዜጎች ለራሳቸው ደህንነት ሲሉ ህጉን እንዲያከብሩ ይጠይቃሉ" አክለሎም "የጦር ኃይሉ እና ደህንነቱ ሰላምና ፀጥታን ለማስከበርና የዜጎችን ደህንነት ለማስከበር ሥራቸውን ያከናውናሉ" ተብሏል።
በካርቱም ጎዳናዎች ላይ የወጡ ተቃዋሚ ሰልፈኞች አል በሽርን ከሰልጣን ለማውረድ የተጠቀሙባቸውን መፈክሮች "ይውረድ፣ ይውረድ" በማለት እንደገና ድምፃቸውን ከፍ አድርገው እያሰሙ ነው።
አል በሽር ዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት በዳርፉር ውስጥ በተፈጸሙ በጦር ወንጀሎችና በሰብአዊ መብት ጥሰት የእስር ማዘዣ ቆርጦ የሚፈልጋቸው ግለሰብ ናቸው።













