ቢን ላዲን ከሞተ በኋላ አልቃይዳ ምን ደረጃ ላይ ይገኛል?

የአልቃይዳ ቡድን መስራች ኦሳማ ቢላዲን ፓኪስታን ውስጥ በአሜሪካ ኃይሎች ከተገደለ ስምንት ዓመት አስቆጠረ። ቡድኑ በዓለማችን ላይ አደገኛ የሚባሉ የጂሃድ ጥቃቶችን ይፈፅም የነበረ ሲሆን በሺዎች የሚቆጠሩ ተዋጊዎችንም ያዝ ነበር።
ቡድኑ ጥቃቶችን ለመፈፀም እና የማይነጥፍ የገንዘብ ምንጭ እንደነበረውም ይታመናል።
ነገር ግን የቡድኑ መሪ ቢን ላዲን ከተገደለ በኋላና አይኤስ የተባለው እስላማዊ ቡድን እየተጠናከረ ሲመጣ የአልቃይዳ ስም እየደበዘዘ ጉልበቱም እየሟሸሸ መጣ።
ታዲያ አልቃይዳ አሁን በምን ደረጃ ላይ ይገኛል? ምን ያህል ተፅዕኖ ፈጣሪ ነው? ምን ያህልስ ለዓለም ደህንነት ያሰጋል?
በዝምታ ማንሰራራት
አይኤስ የእስላማዊ ቡድን በቅርቡ የሚዲያ ገፆችን የተቆጣጠረ ሲሆን አልቃይዳ በበኩሉ ከዓለም እይታ ራሱን ሸሽጎ እያንሰራራ ይገኛል።
ከዚህም በተጨማሪ ቡድኑ ከተለያዩ ቡድኖች ጋር ትብብርን በመፍጠር ራሱን እያሳደገ ይገኛል።
የአሜሪካ የደህንነት መስሪያቤት ባወጣው ወቅታዊ መረጃ የአልቃይዳ መሪዎች "የቡድኑን ዓለም አቀፍ አደረጃጀት እያጎለበተና በምዕራቡ ዓለም ላይ ጥቃት እንዲፈፅሙ እያበረታታ ነው" ብሏል።
የተባበሩት መንግስታት በያዝነው ዓመት መግቢያ ላይ ያወጣው የሽብርተኝነት መረጃ "አልቃይዳ በውስጥ ለውስጥ ራሱን እያደራጀ ከምንግዜውም በላይ ጠንካራ እየሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃም እያዳገ መጥቷል" ይላል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ዓለም አቀፍ ግንኙት
የአሜሪካ ደህንነት ኃይል ተከታታይ የሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃት፣ የቢንላደን መገደልና የአይኤስ ቡድን መጠናከር አልቃይዳ አዳዲስ ዘዴዎችን እንዲጠቀም አስገድደውታል።
አልቃይዳም አሁን ከተለያዩ ቡድኖች ጋር ግንኙነት በመፍጠር በአፍሪካ፣ መካከለኛው ምስራቅና ደቡብ እስያ ቅርንጫፎች አለው።
ለአልቃይዳ መሪነት ራሳቸውን ያስገበሩት አማፂ ቡድኖች በተለያዩ ማህበረሰቦች ውስጥ በስውር የሚንቀሳቀሱ ናቸው።
ከአይኤስ በተቃራኒው አልቃይዳ በሚንቀሳቀስበት አካባቢ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎችን ከማግለል ተቆጥቧል።
በዚህም ስልቱ ከማህበረሰቡ ጋር በመግባባት የአካባቢ ልማት ፕሮጀክቶች ጋር መሳተፍ ጀምሯል።
በአዲሱ የአደረጃጀት ስልቱም አልቃይዳ ማህበረሰብ ተኮር መንገድን እየተጠቀመ ሲሆን፣ ወታደሮቹን "የብዙሃኑን ተቃውሞ" ከሚያነሳሱ ድርጊቶች እንዲቆጠቡ በመተዳደሪያ ህጉ ላይ አስፍሯል።
"ይህንም ተከትሎም ረዳት የሌላቸውን የሚታደግ እና 'የጂሃድ መልካም ሰዎች' በማለት ራሱን አረመኔ ከሆኑት አይኤስ ነጥሎ አስቀምጧል" የምትለው ዶ/ር ኤልሳቤት ካንዳል የፔምብሮክ ኮሌጅ አማካሪ ናት።
አልቃይዳ በ2018 እ.ኤ.አ፣ 316 ጥቃቶችን እንደፈፀመም አርምድ ኮንፍሊክት ሎኬሽን ኤንድ ኤቨንት ዳታ ፕሮጀክት (ACLED) አሳውቋል።
የወደፊቱ የአልቃይዳ መሪ
እ.ኤ.አ በ2015 የአልቃይዳ መሪ የሆኑት አይማን አል ዛዋሃሪ ለቡድኑ መሪነት "የመንጋው መሪ አንበሳ" ብለው አንድ ወጣት አስተውቀዋል።
ወጣቱ የኦሳማ ቢላደን ልጅ ሃምዛ ቢን ላዲን ሲሆን በብዙዎች የወደፊቱ የአልቃይዳ መሪ ተደርጎ ይወሰዳል።
አሜሪካ ሃምዛ ቢን ላዲንን ሽብርተኛ ብላ ሰይማ፣ መገኛውን ለጠቆመ የአንድ ሚሊዮን ዶላር ሽልማት እንደምታበረክት ገልፃለች።
በቅርብ ዓመታት ሃምዛ የአባቱን በቀል ለመመለስ ሲል አሜሪካን ለማጥቃት ትብብር የሚጠይቅ ምስልና የድምፅ መልእክት ለቅቋል።













