"ትራምፕ ከሩስያ ጋር አልዶለቱም"

ሮበርት ሙለር በ2011 የኤፍቢአይ ዳይሬክተር ሆነው ቃለ መሐላ ሲፈጽሙ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ላለፉት ሁለት ዓመታት ጥልቅና ሰፊ ምርመራ ሲካሄድባቸው ነበር፤ ዶናልድ ትራምፕ ላይ። ምርመራው ሂላሪን ያሸነፉት ከሩስያ ጋር ዶልተው ነው ከሚል ጥርጣሬ የተጀመረ ነው። ሩስያ በእርግጥ በ2016ቱ የአሜሪካ ምርጫ እጇን አስገብታ ነበር? ብዙዎች የዚህን ጥያቄ ምላሽ በጉጉት ሲጠብቁ ነበር።

"የሙለር ምርመራ" ተብሎ የሚጠራው ይህ ሂደት የዶናልድ ትራምፕን የቅርብ ረዳቶች ሳይቀር ዘብጥያ እንዲወርዱ ያደረገ ነበር። ግማሾቹ የሕግ ሂደትን በማደናቀፍ፣ ከፊሎቹ በምርመራ ወቅት ዋሽታችኋል፣ ሐቅ መናገር ተናንቋችኋል በሚል እስር ተበይኖባቸው ነበር።

በመጨረሻም ይህ ምርመራ ውጤቱ ትናንት እሁድ ለኮንግረስ ቀርቧል።

የትራምፕ ምርጫ ዘመቻ ከሩስያ ጋር ምንም ዓይነት መመሳጠር አልነበረበትም ብሏል፣ ሪፖርቱ።

ፑቲን ከተራምፕ ጋር በ2017 በጂ20 ስብሰባ ተገናኝተው በመከሩበት ወቅት

የፎቶው ባለመብት, SAUL LOEB/AFP/GETTY IMAGES

ያም ሆኖ ሪፖርቱ ትራምፕ የሕግ ሂደትን ስለ አለማደናቀፋቸው ወይም ከወንጀል ሙሉ በሙሉ ነፃ ስለመሆን አለመሆናቸው ድምዳሜን አይሰጥም።

ሪፖርቱ ለኮንግረሱ የቀረበው በልዩ አቃቢ ሕግ ዊሊያም ባር ፍሬ ሐሳቡ ከተጠናቀረ በኋላ ነበር።

ዶናልድ ትራምፕ የሪፖርቱን መውጣት ተከትሎ "መመሳጠርም ሕግ ማደናቀፍም ብሎ ነገር የለም" የሚል መልዕክት በትዊተር ሰሌዳቸው ላይ ጽፈዋል።

ትራምፕ እሁድ ዕለት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት "በሌለ ነገር ይህን ሁሉ ጊዜ ማጥፋት ያሳፍራል" ብለው ነበር።