አስር ኢትዮጵያዊያን ወደ ደቡብ አፍሪካ ሲጓዙ ዛምቢያ ላይ በቁጥጥር ስር ዋሉ

በህገወጥ መንገድ ወደ ደቡብ አፍሪካ ሲያቀኑ ዛምቢያ ላይ የተያዙት አስር ኢትዮጵያዊያን በእስር ላይ ይገኛሉ።
ስደተኞቹ ባለፈው ሳምንት አርብ ፍርድ ቤት ቀርበው እያንዳንዳቸው ሦስት መቶ ዶላር እንዲከፍሉ ካልሆነ ግን እንደሚታሰሩ እንደተገለፀላቸው ችሎቱ ላይ የኢትዮጵያዊያኑ አስተርጓሚ የነበረችው ብርቱካን ገረመው ለቢቢሲ ገልፃለች።
አስሩም ወንዶች ሲሆኑ ከ18 እስከ 38 የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ናቸው።
ብረቱካን እንደገለፀችው ስደተኞቹ ከታንዛንያ ጋር ዛምቢያን በምታዋስነውና ከዋና ከተማዋ ሉሳካ 750 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ቺንሳሊ በተሰኘችው ትንሽ ከተማ ውስጥ ሲሆን ኢትዮጵያዊያኑ ለቀናት ምግብ ሳያገኙ ልብሳቸው እላያቸው ላይ ተቀዳዶ በከፍተኛ አካላዊ ጉስቁልና ላይ ሆነው ነው የተገኙት። ከተያዙት ስደተኞች መካከልም አንዱ በፅኑ መታመሙ ተነግሯል።
"በኮንቴነር ከኬንያ ታንዛንያ ፤ ከታንዛያ ደግሞ ወደ ዛምቢያ ክልል እንደገቡ ነበር በቁጥጥር ስር የዋሉት" የምትለው ብርቱካን መንገድ ላይ ፖሊስ ሲያስቆማቸው ሾፌሩ እንዳመለጠና ከዚያም ሾፌሩ መኪናውን ነድቶ ወደ ጫካ በመውሰድ ገንዘብ እንደጠየቃቸው እንደነገሯት ገልፃለች።
ብርቱካን ከጉዳዩ ጋር የሚያገናኛት ምንም ነገር ባይኖርም በአካባቢው ኢትዮጵያዊ ሆና በመገኘቷ በማስተርጎም እንድትረዳቸው በአካባቢው የዛምቢያ የፀጥታ ሃላፊዎች በአለቃዋ በኩል መጠራቷን ተናግራለች።
ኢትዮጵያዊያኑ በአስራ አራት ቀናት ውስጥ የተጣለባቸውን የገንዘብ ቅጣት ካልከፈሉ በውሳኔው መሰረት እስሩ እንዲፀናባቸው እንደሚደረግ በፍርድ ቤት ተገልፆላቸዋል።
የተወሰኑት ስደተኞች ደቡብ አፍሪካ ዘመዶች ስላሏቸው እነሱን እንዳነጋገረችና ገንዘብ ከፍሎ ለማስለቀቅ መስማማታቸውን እንዲሁም እራሷ የተቻላትን አድርጋ በቀሩት ጥቂት ቀናት ከእስር እንዲለቀቁ ለማድረግ እየተንቀሳቀሰች መሆኑን ትናገራለች።
ከዚህ ቀደምም በተመሳሳይ ኢትዮጵያዊያን አካባቢው ላይ በቁጥጥር ስር ውለው ሁለት ባልደረቦቿ በተለያየ ጊዜ ተደውሎ ፍርድ ቤት መሄዳቸውን ብርቱካን አስታውሳለች።












