አሜሪካ እና ዩኬ በሶማሊያ ከፍተኛ የኤሌክትሮኒክስ ቪዛ መረጃ ጥሰት እንደሚፈጸም አስጠንቀቁ

የፎቶው ባለመብት, Villa Somalia
በሶማሊያ የኤሌክትሮኒክስ ቪዛ ስርዓት ላይ የተፈጸመ ከፍተኛ የመረጃ ጥሰት የአሜሪካ ዜጎችን ጨምሮ የአስር ሺዎች አመልካቾች የግል መረጃዎችን አጋልጦ ሊሆን እንደሚችል በሶማሊያ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ አስጠነቀቀ።
"ያልታወቁ ጠላፊዎች" የሶማሊያ መንግሥት የኢ-ቪዛ ስርዓት ዘልቀው በመግባት ቢያንስ ከ35,000 ሰዎች የተገኘ መረጃ አደጋ ላይ ሊጥሉ እንደሚችሉ አሳማኝ መረጃዎች እንደደረሱት ገልጿል።
ሐሙስ ዕለት በወጣው የአሜሪካ ኤምባሲ መግለጫ መሠረት በበይነ መረብ ላይ የሚዘዋወሩት ሾልከው የወጡ ሰነዶች ስሞችን፣ ፎቶዎችን፣ የትውልድ ቀናትን፣ የጋብቻ ሁኔታን፣ የቤት አድራሻዎችን እና ኢሜሎችን ያካተቱ ናቸው።
"ይህ የመረጃ ጥሰት ቀጣይነት ያለው ሲሆን ወደ ስርዓቱ የሚያስገቡትን ማንኛውንም የግል መረጃ ሊያጋልጥ ይችላል" ስትል ዩናይትድ ኪንግደምም ተጓዦችን አስጠንቅቃለች።
"ወደ ሶማሊያ ለመጓዝ የሚያስፈልገውን የኢ-ቪዛ ከማመልከትዎ በፊት አደጋዎችን ያስቡበት።"
የሶማሊያ ባለሥልጣናት ስለ ጥሰቱ አስተያየት አልሰጠም። ነገር ግን መንግሥት ይፋዊ ማብራሪያ ሳይሰጥ የቪዛ አገልግሎቱን ከevisa.gov.so ወደ etas.gov.so አዘዋውሮታል።
"የሶማሊያ ኤምባሲ የአንድ ግለሰብ መረጃ የጥሰቱ አካል መሆኑን ማረጋገጥ ባይችልም፣ የሶማሊያ ኢ-ቪዛ ያመለከቱ ግለሰቦች ግን ሊጎዱ ይችላሉ" ሲል የአሜሪካ መግለጫ ገልጿል።
ቢቢሲ የሶማሊያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣንን ምላሽ እንዲሰጥ ቢጠይቅም ምላሽ አላገኘም።
የሶማሊያ አዲሱ ስርዓት ሁሉም ተጓዦች፣ ራሷን እንደ ነጻ አገርነት ካወጀችው የሶማሊላንድ ሪፐብሊክ እና ከፊል ራስ ገዝ ከሆነችው የፑንትላንድ ክልል የመጡትን ጨምሮ፣ የመግቢያ ቪዛ በበይነ መረብ እንደሚያመለክቱ ያስገድዳል።
ተቺዎች እንደሚሉት ተጓዦች በተወሰኑ ክልሎች እስከ እጥፍ የሚደርስ ተጨማሪ ክፍያዎችን ይጠየቃሉ።
እአአ በ1991 ነፃነቷን ያወጀችው ሶማሊላንድ ራሷን በራሷ ተቋማት ብታስተዳድርም ነገር ግን በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና አላገኘችም። ሶማሊያ ክልሉ የሉዓላዊ ግዛቷ አካል እንደሆነች ትከራከራለች።
ተፈጽሟል የተባለው ጥሰት በሞቃዲሾ እና በሐርጌሳ መካከል በሶማሊያ የአየር ክልል ቁጥጥር ላይ ለረጅም ጊዜ የዘለቀውን ውጥረትን አክርሮታል። ሶማሊያ እአአ በ2017 የአየር ክልሏን ሙሉ በሙሉ ስትቆጣጠር ሶማሊላንድ ግን ይህን አምርራ ትቃወማለች።
የሶማሊላንድ ፕሬዝዳንት አብዲራህማን ኢሮ፣ ሶማሊላንድ የሶማሊያን የኢ-ቪዛ ፈቃድ እንደማትቀበል በመግለጻቸው እና አየር መንገዶች ወደ አየር ክልሏ ከመግባታቸው በፊት ከሐርጌሳ ፈቃድ ማግኘት እንዳለባቸው ባዘዙበት ወቅት ውጥረቱ የበለጠ ተባብሷል።
ሆኖም ዋና ዋና አየር መንገዶች የሶማሊያን የኢ-ቪዛ ፈቃድ ያላገኙ ተሳፋሪዎችን ለማጓጓዝ ፈቃደኛ አልሆኑም።
ቅዳሜ ዕለት የሶማሊላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አብዲራህማን ዳሂር አደን እንደገና "ወደ ሶማሊላንድ የሚጓዝ ማንኛውም ሰው ቪዛውን ሲደርስ ያገኛል" ያሉ ሲሆን፣ የሶማሊያ የኤሌክትሮኒክስ ቪዛ ስርዓት ደህንነቱ የተጠበቀ እንዳልሆነ በመግለጽ "የሰዎች መረጃ በአክራሪ ቡድኖች እጅ ሊወድቅ እንደሚችል" በማስጠንቀቅ እንደገና አስጠንቅቀዋል።
ይህ ውጥረት የሶማሊያን ኢ-ቪዛ ባለማያዛቸው ምክንያት ወደ ሶማሊላንድ የሚሄዱ አንዳንድ ተጓዦች በአውሮፕላን ማረፊያዎች ውስጥ እንዲቆዩ አድርጓል።
የሶማሊላንድ የሲቪል አቪዬሽን ሚኒስትር ፉአድ አህመድ ኑክስ ለቢቢሲ እንደተናገሩት በዚህ ዓመት መጀመሪያ ይፋ የተደረጉት መመሪያዎቹ እአአ ኅዳር 10 ጀምሮ ተግባራዊ ሆነዋል።
መመሪያውን የማያከብሩ አየር መንገዶች አቅጣጫቸውን እንዲቀይሩ እንደሚነገራቸው እና በርካታ አውሮፕላኖች አስቀድመው አቅጣጫቸውን እንደቀየሩ ተናግረዋል።
የሶማሊላንድ የአቪዬሽን ሚኒስቴር የአካባቢው የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ለዓለም አቀፍ አብራሪዎች መመሪያ ሲሰጡ የሚያሳይ ተንቀሳቃሽ ምስል አውጥቷል። ይህ እርምጃ የሶማሊላንድን የራስ ገዝነት ማረጋገጫ ተደርጎ በአገር ውስጥ ድጋፎችን አግኝቷል።
ነገር ግን የሶማሊያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን መላውን የአገሪቱን የአየር ክልል የሚሸፍነውን የሞቃዲሾ የበረራ መረጃ ክልል ላይ ብቸኛ የአስተዳደር እና የሕግ ቁጥጥር እንዳለው አጥብቆ ተናግሯል። ሁሉም አውሮፕላኖች ከሞቃዲሾ ውጭ ባሉ ባለስልጣናት የተሰጡ ማናቸውንም መመሪያዎች ችላ እንዲሉ አዟል።
የሶማሊያን እና የዓለም አቀፍ የአቪዬሽን ደንቦችን አለማክበር የደህንነት አደጋዎችን እና "ከባድ የሕግ ጥሰቶችን" ሊያስከትል እንደሚችል አስጠንቅቋል።















