ፕሬዝዳንት ትራምፕ ዩፎዎች እና ባዕድ ፍጡራንን የተመለከቱ መረጃዎችን ይፋ ሊያደርጉ ነው

የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

የፎቶው ባለመብት, Reuters

የንባብ ጊዜ: 2 ደቂቃ

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የመከላከያ ሚኒስቴራቸውን ጨምሮ ሁሉም የመንግሥት ተቋማት ከሌሎች ዓለማት የሚመጡ እንግዳ ፍጥረታትን በተመለከተ ያሏቸውን መረጃዎች ይፋ ለማድረግ "የመለየት ሥራ እንዲያከናውኑ" ማዘዛቸውን ገለጹ።

ትራምፕ ይህንን ትዕዛዝ መስጠታቸውን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ይፋ ያደረጉት፤ የቀድሞው ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ከዚህ ጋር በተያያዘ ምሥጢራዊ መረጃን አውጥተዋል ብለው ከከሰሱ በኋላ ነው።

ኦባማ ባለፈው ሳምንት በአንድ ፖድካስት ላይ በሰጡት ቃለ መጠይቅ "ባዕድ ፍጥረታት አሉ" ብለው ነበር።

ኦባማ "ምሥጢር ይፋ ማድረግ አልነበረበትም" ሲሉ በኤርፎርስ ዋን አውሮፕላን ውስጥ ለጋዜጠኞች የተናገሩት ፕሬዝዳንቱ፤ "ትልቅ ስህተት ሠርቷል" ሲሉም ወቅሰዋል።

ትራምፕ ባዕድ ፍጥረታት አሉ ወይ በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት መልስ፤ "ስለመኖር አለመኖራቸው የማውቀው ነገር የለም" ብለዋል።

የቀድሞው ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ፤ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ በተለቀቀ ፖድካስት ላይ ከሌላ ዓለም የሚመጡ ባእድ ፍጡራን አሉ ብለዋል።

"ፍጡራኑ አሉ፤ እውነት ናቸው። ነገር ግን እኔ አላየኋቸውም" በማለት "በሴራ ትንተና እንደሚባለው ከአሜሪካ ፕሬዝዳንት የሚደበቅ ምሥጢር ካልኖረ በስተቀር ምንም ዓይነት ከመሬት በታች የሚገኝ ምሥጢራዊ ስፍራ የለም" ብለዋል።

ይህ የቀድሞው ፕሬዝዳንት አስተያየት መነጋገሪያ ከሆነ በኋላ ኦባማ በሰጡት ማብራሪያ አጽናፈ ዓለም (ዩኒቨርስ) ካለው ስፋት የተነሳ ከመሬት ባሻገር ሕይወት እንዳለ እንደሚያስቡ አስረድተዋል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

ከአውሮፓውያኑ 2009-2017 የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የነበሩት ኦባማ በኋላ ላይ በኢንስታግራም ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ፤ "ፕሬዝዳንት በነበርኩበት ጊዜ ከሌላ ዓለማት የመጡ ባዕድ ፍጡራን ምንም ዓይነት ግንኙነት ማድረጋቸው የተመለከተ መረጃ አላየሁም" ሲሉ አብራርተዋል።

ባራክ ኦባማ ቃለ ምልልሱን ባደረጉበት ጊዜ ምሥጢራዊ መረጃን መሠረት ስለማድረጋቸው የተጠቀሰ ነገር የለም። ቢቢሲ ኦባማ አስተያየታቸውን እንዲሰጡ ጠይቋል።

በዲሞክራቱ ኦባማ እና በሪፐብሊካኑ ትራምፕ መካከል ለረጅም ጊዜ የዘለቀ ፖለቲካዊ ባላንጣነት መኖሩ ይታወቃል።

ምንም እንኳን በርካታ ሰዎች ባዕድ ፍጡራን ስለመኖራቸው ቢያምኑም ፕሬዝዳንት ትራምፕ ስለእነዚህ ፍጡራን ተናግረው አያውቁም። ሐሙስ ዕለት በኤርፎርስ ዋን አውሮፕላን ውስጥ ሆነው በሰጡት ቃለ ምልልስ "በጉዳዩ ላይ አስተያየት የለኝም" ብለዋል።

ከሰዓታት በኋላ ግን ትሩዝ በተባለው የማኅበራዊ ሚዲያቸው ላይ በጉዳዩ ላይ "ካለው ከፍተኛ ፍላጎት የተነሳ"፤ "ከባዕዳን ፍጡራን፣ በሌሎች ዓለማት ሕይወት ስለመኖሩ፣ ስላልታወቁ የአየር ላይ ክስተቶች፣ ምንነታቸው ስላልታወቁ በራሪ አካላት (ዩፎ)" እና ስለሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮች ያሉ መረጃዎች ይፋ እንዲሆኑ እንደሚያዝዙ ገልጸዋል።

ከዚህ ቀደም የአሜሪካ መከላከያ መሥሪያ ቤት ምሥጢራዊ ፕሮግራም እያካሄደ ነው የሚል መረጃ ከወጣ በኋላ የዩፎዎች ጉዳይ መነጋገሪያ ጉዳይ ሆኖ ነበር።

በአውሮፓውያኑ 2017 ፓይለቶች እና በሰማይ ላይ እንግዳ ነገሮችን መመልከታቸውን ሪፖርት ያደረጉ የጦር ሠራዊት አባላት ለምርመራ ቃላቸውን እንዲሰጡ ተደርጎ ነበር።

በ2022 ደግሞ ከ50 ዓመታት በኋላ የአሜሪካ ምክር ቤት ለመጀመሪያ ጊዜ በዩፎ ጉዳይ ላይ ምስክርነቶችን አድምጧል።

ከዚህ ጋር የተያያዙ መረጃዎችን ግልጽ ለማድረግ ቃል የመከላከያ መሥሪያ ቤቱም፤ ስለዩፎዎች የሚያገኛቸውን መረጃዎች የሚያሰባስብ እና ሪፖርት የሚያደርግ ጽህፈት ቤት አቋቁሟል።

የአሜሪካ ተወካዮች ምክር ቤት ኮሚቴ ጉዳዩን በተመለከተ ባደረገውን ምርመራ ይህ ነው የሚባል ማስረጃም ሆነ ባዕድ አካላት ስለመኖራቸው የሚያረጋግጥ መረጃ ሳያገኝ ቀርቷል።

ከሁለት ዓመት በፊት የወጣው ሪፖርት ደግሞ የአሜሪካ መንግሥት ምንም ዓይነት ባዕድ አካላትን ስለማግኘቱ የሚያመለክት "መረጃ የለም" ብሏል።

ዩፎ እንደታየ የተነገሩ ጉዳዮች የሚታወቁ ቁሶች ናቸው ሲልም ማረጋገጫ አለመገኘቱን ጠቅሷል።