ኢትዮጵያን ጨምሮ በበርካታ የአፍሪካ አገራት የእርሻ መሬት ግዢን እያስፋፋች ያለችው የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ

አህመድ ዳልሙል አል ማክቱም ከዛምቢያ ፕሬዝዳንት ጋር

የፎቶው ባለመብት, HAKAINDEHICHILEMA/FACEBOOK

የምስሉ መግለጫ, አህመድ ዳልሙል አል ማክቱም ከዛምቢያ ፕሬዝዳንት ጋር

ባለፉት አስርት ዓመታት የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በፖሊሲዋ በአፍሪካ የኢኮኖሚ የበላይነት ለመያዝ ፍላጎቷን ታንፀባርቃለች።

ይህም ፍላጎቷ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶችን ጨምሮ የንግድ ልውውጧን እና የወደብ አስተዳደሯን ማሳደግን ያካትታል።

የባህረ ሰላጤዋ አገር በተጨማሪም በአፍሪካ ግዙፍ የመሬት ግዢን እንደ ስልት እየተከተለች ሲሆን፤ ትላልቅ የእርሻ መሬቶችን፣ ለቅንጡ ቱሪዝም የሚሆኑ የዱር እንስሳት መገኛ አካባቢዎችን እና የባሕር ዳርቻዎችን በእጇ አስገብታለች።

በዚህም ሳትገታ ለካርቦን ማምረቻ የሚሆን ሚሊዮኖች ሄክታር ጫካዎችን የግሏ አድርጋለች።

ይሁን እንጂ ሰፊ ሽፋን ያለው እና በአካባቢው ማኅበረሰብ ላይ ጉዳት ያስከትላል በሚል ይህ አገሪቱ እንቅስቃሴ በተቺዎች እና በአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች ዘንድ መሬት ነጠቃ ስልት ተደርጎ ታይቷል።

የመሬት ግዢዎቹ መሬቱን በሸጡት የአፍሪካ አገራት የሀብት እጦት፣ የምግብ ዋስትና ስጋት፣ ነባር የአገሬውን ሰዎች ማፈናቀል፣ ግጭት ማባባስ እና የአካባቢ ጥበቃ "አስመሳይነት" የመሰሉት አሉታዊ አንደምታዎች አሉት።

እ.አ.አ የ2023 የዓለም ባንክ መረጃ እንደሚያሳየው 0.7 በመቶ ብቻ የሚሆነው የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መሬት የሚታረስ ነው።

ከ85 እስከ 90 በመቶ የሚሆነውን ምግቧን ከውጭ የምታስገባው አቡ ዳቢ በ2018 'ብሔራዊ የምግብ ደኅንነት 2051 ስትራቴጂ' የተባለ ዓመቱን ሙሉ ለመላው ዓለም ደኅንነቱ የተጠበቀ፣ የተመጣጠነ እና በቂ ምግብ በማቅረብ ረሃብን ዜሮ ለማድረስ ዓላማ የሰነቀ እቅድ ይፋ አድርጋለች።

ባለፉት አስርት ዓመታት የባህረ ሰላጤው አገር ከአፍሪካ አገራት ጋር በተለይም በምግብ ዘርፍ ያላትን የንግድ ልውውጥ በፍጥነት አስፋፍታለች።

ይህ ጥረት የምግብ ምርቶችን ከማግኘት አገሪቱን የዓለም የምግብ ንግድ ማዕከል ወደ ማድረግ ወዲያ የተስፋፋ ሲሆን፤ በአፍሪካ የመሬት ግዢዋን እንድታስፋፋም መንገዱን ጠርጓል።

የግዢ ስምነቶቹ በአብዛኛው ከንጉሳዊያን ቤተሰቦች ጋር ግንኙነት ባላቸው ኩባንያዎች በኩል የተፈፀሙ ናቸው።

እነዚህ ኩባንያዎች በአፍሪካ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የግብርና ክንድ ሆነዋል።

ኤዲኪው፣ አል ዳህራ፣ አል ኩድራ ሆልዲንግስ፣ ኤሊት አግሮ ፕሮጄክትስ፣ አል ርዋንቢ፣ ጅናን ኢንቨስትመንትስ፣ ኢንተርናሽናል ሆልዲንግ ካምፓኒ እና አቡ ዳቢ ኢንቨስትመንት ኦቶሪቲ በዋናነት ተጠቃሽ ናቸው።

አቡዳቢ ባለፉት ዓመታት ከኢትዮጵያ፣ ግብፅ፣ ኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ አንጎላ፣ ሞሮኮ፣ ማዳጋስካር፣ ናምቢያ፣ ሴራ ሊዮን እና ሱዳንን ጨምሮ ከበርካታ አፍሪካ አገራት የእርሻ መሬቶችን ገዝታለች።

ኢትዮጵያ እና ኤምሬትስ

ፋርምላንድ ግራብ ዶት ኦርግ የተባለው ድረ ገፅ የኤምሬትስ 'ኢሊት አግሮ ፕሮጄክትስ' የተባለው ኩባንያ በኢትዮጵያ ስንዴ ማምረት ለመጀመር ዕቅድ እንዳለው ከሁለት ዓመት በፊት ዘግቧል።

ኩባንያው ስንዴ ላይ እየጨመረ ባለው ፍላጎት ምክንያት በኢትዮጵያ ለማምረት እያጠና መሆኑን የገለፀ ሲሆን፤ የስንዴ ምርቱ ወደ ኤምሬትስ የሚላክ እና ለኢትዮጵያ ገበያ የሚቀርብ መሆኑን ጠቁሟል።

እ.አ.አ ከ2018 ወዲህ ኢትዮጵያ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን በንግድ፣ ኢንቨስትመንት እና በደኅንነት ትብብር አጠናክረዋል።

ኢትዮጵያ ለኤምሬትስ በአፍሪካ ቀንድ ዋነኛ አጋር ስትሆን ግንኙነታቸው ዘርፈ ብዙ እና ስልታዊ ነው።

በተለይም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ አገራቱ ዲፕሎማሲያዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና የደኅንነት ግንኙነታቸውን በከፍተኛ የመሪዎች ጉብኝት፣ በንግድ እና ኢንቨስትመንት አሳድገዋል።

በኬንያ የምግብ ዋስትና ፕሮጄክት

ባለፈው ሐምሌ 2025 አል ዳህራ በ180 ሺህ ኤከር መሬት ላይ ምግብ ለማምረት የ96.7 ሚሊዮን ዶላር የመግባቢያ ስምምነት ከኬንያ ፈፅሟል።

የኬንያ የግምጃ ቤት ሹም ክሪስ ኪፕቶ ስምምነቱ "የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ያጠናክራል" ብለዋል።

የጋላና ኩላሉ ፕሮጄክት በድርቅ እና ጎርፍ ችግር ውስጥ ለገባችው የምሥራቅ አፍሪካዊቷ አገር የምግብ ዋስትናን ለማሳደግ በ2013 ነበር የተቋቋመው።

80 በመቶው የኬንያ መሬት በከፊል እና ሙሉ ለሙሉ የሚታረስ ነው። 20 ሚሊዮን የሚሆኑ ኬንያዊያን ግን የምግብ ዋስትና የሌላቸው መሆኑን ዘገባዎች ያመላክታሉ።

ከኡጋንዳ ጋር የምግብ ንግድን ማስፋፋት

ባለፈው መስከረም ኡጋንዳ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በግብርናው ዘርፍ በጋራ ለመስራት የትብብር አማራጮችን እያማተሩ መሆኑን የኡጋንዳ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

ዘገባው ትብብሩ በአገራቱ መካከል ያለውን የምግብ የንግድ ልውውጥ በ30 በመቶው እንደሚያሳድግ ጠቅሷል።

ኡጋንዳ ወደ ገባህረ ሰላጤዋ አገር የምትልከው ምግብ ከ50 ሚሊዮን ዶላር የላቀ ነው።

ውጥኑ በእንተቤ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ አቅራቢያ የኡጋንዳ ምርቶች የሆኑትን ዝንጅብል፣ ማንጎ፣ አቩካዶ፣ አናናስ፣ እንቁላል እና ሌሎችን ምርቶች ለማቀዝቀዝ የሚውል በ50 ሚሊዮን ዶላር የሚገነባ ማከማቻን ያካትታል።

በ2018 ኡጋንዳ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በዓለም የመጀመሪያ ሆነውን የግብርና ነፃ የንግድ ቀጣና ለመመስረት የተስማሙ ሲሆን፤ በ2,500 ኤከር መሬት ላይ የኤምራቲ የግል ኩባንያ በምግብ ማምረት ላይ መዋዕለ ነዋዩን እንዲያፈስ ይፈቅዳል።

የቴምር እና ወይን ፍሬ ማሳ በናምቢያ

በ2017 የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ኩባንያ አራት የወይን ፍሬ ማምረቻ እርሻዎችን ከናምቢያ የግል ኩባንያ ገዝቷል።

እርሻዎቹ በደቡብ አፍሪካ ድንበር አቅራቢያ የሚገኙ ናቸው።

በ2011 የናምቢያ የልማት ኮርፖሬሽን እና መቀመጫውን አቡ ዳቢ ያደረገው አል ዳህራ የወይን ፍሬ እና የቴምር እርሻ በ220 ሄክታር ላይ ለመመስረት ትብብር መስርተዋል።

የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ኩባንያ እና ግብፅ ስምምነት ሲፈራረሙ

የፎቶው ባለመብት, ADQ

የምስሉ መግለጫ, በ2024 ኤዲኪው የተባለው ኩባንያ በግብፅ የባሕር ዳርቻ ለማልማት የ35 ቢሊዮን ዶላር ስምምነት አስሯል

ቅንጡ ቱሪዝም

የእርሻ መሬቶችን ከመግዛት ባለፈ አቡ ዳቢ ለቱሪዝም እና አደን የሚውሉ ግዙፍ መሬቶችን እየተከራየች ነው።

በ2024 ኤዲኪው የተባለው ኩባንያ በግብፅ የባሕር ዳርቻ ከተማ የሆነችውን ራስ ሄክማ ለማልማት የ35 ቢሊዮን ዶላር ስምምነት አስሯል።

የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በታንዛኒያ ለቅንጡ የአደን ቱሪዝም የሚውል የዱር እንስሳት ኮሪደር ለመመስረት ፍላጎት እንዳሳየች የሚጠቁሙ ሪፖርቶች ወጥተዋል።

ውጥኑ እውን ከሆነ ከ70 ሺህ በላይ ነባር የአገሬው ተወላጅ የሆኑትን የማሳይ ጎሳዎችን የሚያፈናቅል እና የማሳይ ቀጭኔን ጨምሮ ሌሎች የዱር እንስሳት ዝርያዎችን አደጋ ላይ የሚጥል ነው በሚል ስጋት አሳድሯል።

በ2022 የታንዛኒያ መንግሥት በአገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል 1,500 ስኩዌር ኪሎ ሜትር የሚሸፍን መሬት መሰረቱን የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ላደረገው ኦቴርሎ ቢዝነስ ኮርፖሬሽን ለተባለ ኩባንያ ለማከራየት የያዘውን እቅድ ይፋ አድርጓል።

የደቡብ አፍሪካው ሜል ኤንድ ጋርዲያን ጋዜጣ በዚህ መሬት አካባቢ 31 የማሳይ ማኅበረሰቦች ከመንግሥት ኃይሎች ጋር ተጋጭተው መጉዳታቸውን እና ከ2,160 የሚሆኑት ደግሞ ወደ ኬንያ መሸሻቸውን ዘግቧል።

የማሳይ ጎሳዎች

የፎቶው ባለመብት, Emirates Leaks

የምስሉ መግለጫ, ዩኤኢ ለመገንባት ያቀደችው የአደን ቱሪዝም ኮሪደር ከ70 ሺህ በላይ ነባር የአገሬው ተወላጅ የሆኑትን የማሳይ ጎሳዎችን የሚያፈናቅል ነው

በተመሳሳይ ሁኔታ በ2023 በኬንያ ለተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የካርቦን መሬት መሸጥን ተከትሎ የአደን ማኅበረሰብ የሆኑት ኦጊክ አባላት በማው ጫካ ከመሬታቸው ተባረዋል።

ከዚህ ባለፈ አቡ ዳቡ ለካርቦን ልቀት መፍትሔ በሚል "ዩናይትድ ኪንግደምን Yሚያክል" በሚሊዮኖች የሚቆጠር ሄክታር መሬት ገዝታለች።

ኬንያ፣ ዛምቢያ፣ ዚምባቡዌ፣ ታንዛኒያ፣ ላይቤሪያ፣ ኮሞሮስ እና ኒጀር የዱባይ ንጉሳዊ ቤተሰብ ባለቤትነት በተያዘ ኩባንያ ጋር ውል በማሰር ተጠቃሽ ናቸው።

ይሁን እንጂ በዚህ ረገድ የአቡ ዳቢ እንቅስቃሴ ከውዝግብ እና ትችት አላመለጠም።

የካርቦንን ልቀት ለመቀነስ በሚል የበለፀጉ አገራት የራሳቸውን ብክለት ሳይቀንሱ አሻራቸውን ለማሳረፍ ከሌሎች አገራት የሚገዡት መሬት "የይስሙላ" እርምጃ ነው በሚል የሚተች ሲሆን፤ ነዳጅ አምራቿ አቡ ዳቢም ይህን ፈለግ በመከተሏ ከትችት አላመለጠችም።