የቀድሞው የሰላም ሚኒስቴር ዲኤታ አቶ ታዬ ደንደአ ከእስር ተፈቱ

ፍርድ ቤት በወሰነላቸው መሠረት ከእስር ቤት በዋስ ሲወጡ በፀጥታ ኃይሎች ተይዘው አንድ ሌሊት ያሳለፉት አቶ ታዬ ደንደአ ተለቀው ወደ ቤታቸው መመለሳቸው ባለቤታቸው ተናገሩ።
የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የቀድሞው የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣን የነበሩት አቶ ታዬ ለወራት ከቆዩበት እስር በዋስ እንዲወጡ ከፈቀደ በኋላ አስፈላጊውን ሂደት አሟልተው ከማረሚያ ቤት ሲወጡ ነበር በድጋሚ የተያዙት።
ረቡዕ አመሻሽ ላይ ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሲወጡ በር ላይ በተጠበቋቸው የፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ስር ውለው ወዳልታወቀ ቦታ ተወስደው የነበሩት አቶ ታዬ ደንደአ ዛሬ ሐሙስ ኅዳር 26/2017 ዓ.ም. ዕኩለ ቀን ላይ ተለቀው መኖሪያ ቤታቸው መግባታቸውን ባለቤታቸው ወ/ር ስንታየሁ ዓለማየሁ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
አቶ ታዬ ፍርድ ቤት ከእስር በዋስ እንዲለቀቁ ከወሰነላቸው በኋላ ቢለቀቁም በደኅንነት እና በፌደራል ፖሊስ አባላት ተይዘው ወደማይታወቅ ስፍራ መወሰዳቸውን ባለቤታቸው ለቢቢሲ መናገራቸው ይታወሳል።
አቶ ታዬ አንድ ሌሊት ከቤተሰባቸው ተለይተው ካሳለፉ በኋላ ዛሬ ሐሙስ ምሳ ሰዓት ላይ ከፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ ተለቅቀው፣ ሰባት ሰዓት አካባቢ መኖሪያ ቤታቸው መግባታቸውን ባለቤታቸው ለቢቢሲ አረጋግጠዋል።
አቶ ታዬ ደንደአ በዋስ እንዲለቀቁ ፍርድ ቤት መወሰኑን ተከትሎ ትናንት ረቡዕ ከሰዓት በኋላ ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ቢለቀቁም ከበር ላይ ‘በደኅንነት አባላት እና የፌደራል ፖሊስ መለያ በለበሱ ኃይሎች’ መኪና ውስጥ እንዲገቡ ተደርገው ተወስደው ነበር።
የቀድሞ የሰላም ምክትል ሚኒስትር እና የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አባል አቶ ታዬ ደንደአ በዋስ እንዲለቀቁ የወሰነው የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ሰኞ፣ ኅዳር 23/2017 ዓ. ም. በዋለው ችሎት ነበር።
ትናንት ኅዳር 25/2017 ዓ. ም. አቶ ታዬ በዋስ ይለቃቀሉ በሚል በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሲጠባበቁ እንደነበረ የተናገሩት የአቶ ታዬ ባለቤት ወ/ሮ ስንታየሁ ከሰዓት በኋላ ወደ 11 ሰዓት ገደማ ላይ አቶ ታዬ ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤቱ በር ላይ መወሰዳቸውን በወቅቱ ወደየት እንደተወሰዱ ማወቅ እንዳልቻሉ ተናግረው ነበር።
አቶ ታዬ ከማረሚያ ቤቱ ከመውጣታቸው በፊት በአካባቢው “ሲቪል የለበሱ እና ማስክ ያደረጉ ሁለት የደኅንነት አባላት እንዲሁም ሌሎች የታጠቁ ሰዎችም ነበሩ። የፌደራል ፖሊስ ዩኒፎርም የለበሱም ነበሩ” ያሉት ባለቤታቸው “ተለቆ ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በር ሊወጣ ሲል ውጭ ላይ የነበሩት ያዙት” ሲሉ የተከሰተውን ለቢቢሲ አስረድተዋል።
ከእስር ቤት በር ላይ ከተወሰዱ በኋላ ሐሙስ ማለዳ አቶ ታዬን በፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ ሄደው ማግኘታቸውን ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን የገለፁት ባለቤታቸው፣ ከቀኑ 6፡00 ሰዓት አካባቢ ተለቅቀው ቤታቸው መግባታቸውን ለቢቢሲ አረጋግጠዋል።
የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት አቶ ታዬ ደንደአ 20 ሺህ ብር የዋስትና ገንዘብ በማስያዝ ወይም በዋስ እንዲፈቱ ብያኔ ማሳለፉ ይታወሳል።
ባለፈው ዓመት ከሥልጣን ከተነሱ በኋላ ለእስር የተዳረጉት አቶ ታዬ፣ ሁከትና ብጥብጥ በማነሳሳት፣ ፀረ-ሰላም ኃይሎችን በመደገፍ እንዲሁም የጦር መሣሪያ ሕጉን በመተላለፍ ወንጀሎች ተከሰው ነበር።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የሕገ መንግሥትና ሕገ መንግሥት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች ችሎት ከዚህ ቀደም ከሦስቱ ክሶች መካከል በሁለቱ፣ ሁከት እና ብጥብት በማነሳሳት እና የፀረ- ሰላም ኃይሎችን ድጋፍ ማድረግ ክሶች በነጻ አሰናብቷቸው ነበር።
የጦር መሣሪያ ወንጀሎችን በተመለከተ የቀረበባቸውን ክስ እንዲከላከሉ ፍርድ ቤቱ በዚያኑ ችሎት ውሳኔ ያሳለፈ ሲሆን አቶ ታዬ ጉዳዩን እናውቃለን የሚሉ አምስት የመንግሥት ባለሥልጣናትን ለምስክርነት ጠርተው ነበር።
በምስክርነት ካቀረቧቸው መካከል በቅርቡ ከኃላፊነታቸው የተነሱት የቀድሞው የሰላም ሚኒስትር አቶ ብናልፍ አንዷለም እና የፌደራል ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር መላኩ ፈንታ ምስክርነታቸውን መስጠታቸው ይታወሳል።
በቀሪዎቹ የመንግሥት ባለሥልጣናት ምስክርነት ለመስማት ፍርድ ቤቱ ለታኅሣሥ 3/2017 ዓ. ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
አቶ ታዬ በምስክርነት ቀርበው ያስረዱልኝ ካሏቸው መካከል የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ይገኙበታል።
ዐቃቤ ሕግ በአቶ ታዬ ደንደአ ላይ ሦስት ተደራራቢ ክሶችን የመሠረተው ባለፈው ዓመት ሚያዚያ 2016 ዓ. ም. ነበር።
አቶ ታዬ ባለፈው ዓመት ታኅሣሥ ወር መጀመሪያ ላይ በተደረገባቸውም ክትትል መንግሥት ሸኔ እያለ ከሚጠራው የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት አመራሮች ጋር ግንኙነት በመፍጠር “መንግሥትን ለመጣል ሲያሴሩ” በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የፀጥታ እና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል መግለጹ ይታወሳል።
አቶ ታዬ በአገሪቱ ስላለው የሰላም ሁኔታ እና በመንግሥት ውስጥ ስላሉ ጉዳዮች ለመገናኛ ብዙኃን በመናገር እንዲሁም በማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ ሐሳባቸውን በመግለጽ የሚታወቁ ሲሆን፣ በአገሪቱ የሚካሄደውን ግጭት በተመለከተ ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ላይ መንግሥትን ከተቹ በኋላ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሥልጣናቸው ተሰናብተዋል።
ይህንንም ተከትሎ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ላይ ጠንከር ያለ ትችት እና ክስ በሰነዘሩበት ምሽት በፀጥታ ኃይሎች ከቤታቸው ተወስደው አንድ ዓመት ለሚጠጋ ጊዜ በእስር ላይ ቆይተው ነው በፍርድ ቤት ውሳኔ በዋስ ሊወጡ የነበረው።
የአቶ ታዬ ደንደአ አሁን ያሉበትን ቦታ እና ሁኔታ ከተመለከተ ፖሊስ እስካሁን ያለው ነገር የሌለ ሲሆን፣ ቤተሰባቸውም የሚያውቀው ነገር እንደሌለ ባለቤታቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል።















