በቴህራን እና በሌሎች የኢራን ከተሞች ከፍተኛ የመንግሥት ተቃውሞዎች ተካሄዱ

የፎቶው ባለመብት, UGC
ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የተቃውሞ ሠልፈኞች በኢራን ዋና ከተማ እና በሌሎች ከተሞች መከናወናቸውን በበይነመረብ እየተዘዋወሩ ከሚገኙ ቪዲዮዎች ለማወቅ ተችሏል። ተቃውሞው ካለፉት ዓመታት ትልቁ እንደሆነ ተነግሮለታል።
ሐሙስ ምሽት በቴህራን እና በሁለተኛው ከተማ ማሽሃድ የተካሄዱትን የተቃውሞ ሠልፎች የጸጥታ ኃይሎች ለመበተን አለመሞከራቸውን በቢቢሲ ፐርሺያ የተረጋገጡ ቪዲዮዎች አሳይተዋል።
በመላ አገሪቱ ኢንተርኔት መዘጋቱም ተዘግቧል።
ተቃዋሚዎች የኢራን መንፈሳዊ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ከሥልጣን እንዲለቁ እና ደጋፊዎቻቸው ወደ ጎዳና እንዲወጡ ያሳሰቡትን የቀድሞ ሻህ ልጅ ሬዛ ፓህላቪ ቦታውን እንዲረከቡ ሲጠይቁ እንደነበር ከቪዲዮዎቹ ድምጽ ለመረዳት ተችሏል።
በኢራን የገንዘብ ምንዛሪ መውደቅ ምክንያት የተቀሰቀሰው ቁጣ ለ12ኛ ተከታታይ ቀን የቆየ ሲሆን በኢራን 31 ግዛቶች ውስጥ በሚገኙ ከ100 በላይ ከተሞችና መንደሮች ተሰራጭቷል ሲሉ የሰብዓዊ መብት ቡድኖች ተናግረዋል።
በአሜሪካ የሚገኘው ሂውማን ራይትስ አክቲቪስት ኒውስ ኤጀንሲ (ህራና) አምስት ልጆችን ጨምሮ ቢያንስ 34 ተቃዋሚዎች እና ስምንት የጸጥታ ኃይሎች መገደላቸውን እና 2,270 ተቃዋሚዎች መያዛቸውን አስታውቋል።
በኖርዌይ የሚገኘው የኢራን የሰብአዊ መብቶች ድርጅት (አይኤችአር) በበኩሉ ስምንት ልጆችን ጨምሮ ቢያንስ 45 ተቃዋሚዎች በጸጥታ ኃይሎች መገደላቸውን ተናግሯል።
ቢቢሲ ፐርሺያ የ22 ሰዎችን ሞት ማንነትን ሲያረጋግጥ የኢራን ባለሥልጣናት ደግሞ ስድስት የጸጥታ ኃይሎች ሕይታቸው ማለፉን ሪፖርት አድርገዋል።
ሐሙስ ምሽት በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተለጠፉ እና በቢቢሲ ፐርሺያ የተረጋገጡ ቪዲዮዎች በአገሪቱ ሰሜን ምሥራቅ ማሽሃድ ከተማ በሚገኝ ዋና መንገድ ላይ ብዙ ተቃዋሚዎች ሲንቀሳቀሱ አሳይተዋል።
"ሻህ ለዘላለም ይኑር" እና "ይህ የመጨረሻው ጦርነት ነው! ፓህላቪ ይመለሳል" የሚሉ ድምጾች ተደጋግመው ተሰምተዋል። በአንድ አጋጣሚ ደግሞ በርካታ ሰዎች የደህንነት ካሜራዎችን ሲያነሱ ታይተዋል።
በበይነመረብ ላይ በተለጠፈ ሌላ ቪዲዮ ደግሞ በምስራቅ ቴህራን በሚገኝ አንድ መንገድ ላይ ብዙ ተቃዋሚዎችን ሲንቀሳቀሱ አሳይቷል።
ከዋና ከተማዋ ሰሜናዊ ክፍል ለቢቢሲ ፐርሺያን በተላከ ቪዲዮ ላይ ተቃዋሚዎች "ይህ የመጨረሻው ዘመቻ ነው! ፓህላቪ ይመለሳል" ሲሉ ተደምጠዋል። በሰሜን ቴህራን ደግሞ ተቃዋሚዎች ከጸጥታ ኃይሎች ጋር ከተጋጨ በኋላ "የማይከበር" እና "አትፍሩ፣ ሁላችንም አንድ ላይ ነን" ሲሉ ታይተዋል።
በኢስፋሃን ከተማ ተቃዋሚዎች "ሞት ለአምባገነኑ" ሲሉ፤ በሰሜናዊው የባቦል ከተማ "ሻህ ለዘላለም ይኑር" እና በሰሜን ምዕራብ ታብሪዝ ከተማ ደግሞ "አትፍሩ፣ ሁላችንም አንድ ላይ ነን" ሲሉ ታይተዋል።
ተቃውሞዎች የተካሄዱት አባታቸው በ1979 የእስልምና አብዮት ከስልጣን የተወገዱትና በዋሽንግተን ዲሲ የሚኖሩት ሬዛ ፓህላቪ ኢራናውያን "በአንድነት ወደ ጎዳናዎች እንዲወጡና ጥያቄ እንዲያሰሙ" ጥሪ ካቀረቡ በኋላ ነው።
ፓህላቪ በኤክስ ላይ "በሚሊዮን የሚቆጠሩ ኢራናውያን ዛሬ ማታ ነፃነታቸውን ጠይቀዋል" ያሉ ሲሆን ተቃዋሚዎቹን "ደፋሮች" ሲሉ ገልጸዋቸዋል።
የአሜሪካን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ "አገዛዙን ተጠያቂ ስላደረጉ" አመስግነው የአውሮፓ መሪዎችም ተመሳሳይ አካሄድ እንዲከተሉ ጥሪ አቅርበዋል።
ፓህላቪ አርብ ምሽት ጀምሮ ተቃውሞዎቹ ድምጻቸውን ማሰማት እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል።
የኢራን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን የሐሙሱን ተቃውሞ መጠን ዝቅ አድርጎ አቅርቦታል። በአንዳንድ ቦታዎች ተቃውሞዎች እንዳልነበሩ በመጥቀስ ባዶ መንገዶችን የሚያሳዩ ቪዲዮዎችን አሳይቷል።

የፎቶው ባለመብት, X
የኢንተርኔት ተቆጣጣሪው ኔትብሎክስ በበኩሉ መለኪያዎቹን መሠረት በማድረግ ኢራን "የኢንተርኔት መቋረጥ ውስጥ እንዳለች" ያሳያሉ ብሏል።
"ይህ ክስተት በመላ አገሪቱ ተቃውሞዎችን ዒላማ ያደረጉ ተከታታይ የዲጂታል ሳንሱር እርምጃዎችን ተከትሎ የተከሰተ ሲሆን ሕዝቡ በአስቸጋሪ ጊዜ ውስጥ የተግባቦት መብቱን ያደናቅፋል" ሲል አስጠንቅቋል።
በምዕራባዊው የኢላም ግዛት ውስጥ በምትገኘው ሎማር "መድፍ፣ ታንኮች፣ ርችቶች፣ ሙላዎች መሄድ አለባቸው" ሲሉ ተደምጠዋል። በሌላ ቪዲዮ ደግሞ ተቃዋሚዎች የተሰበረ የሚመስል ባንክ አጠገብ ሆነው ወረቀት ሲወረውሩ ታይተዋል።
በኢላም ውስጥ በሚገኙ በርካታ የኩርድ ከተሞች እንዲሁም በከርማንሻህ እና በሎሬስታን ግዛቶች ውስጥ ብዙ የተዘጉ ሱቆች ተዘግተዋል።
ሱቆች የተዘጉት ተቃዋሚዎች ላይ ለተፈጸመው እርምጃ ምላሽ ለመስጠት በስደት ላይ ያሉ የኩርድ ተቃዋሚ ቡድኖች አድማ እንዲደረግ ጥሪ ከቀረበ በኋላ ነው።
በኢላም፣ በከርማንሻህ እና በሎሬስታን ቢያንስ 17 ተቃዋሚዎች በጸጥታ ኃይሎች መገደላቸውን እና ብዙዎቹ የኩርድ ወይም የሎር ጎሳ አባላት እንደነበሩ የኩርድ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ቡድን የሆነው ሄንጋው ገልጿል።
ረቡዕ ዕለት በምዕራብ ኢራን በሚገኙ በርካታ ከተሞችና በሌሎች ክልሎች በተቃዋሚዎችና በጸጥታ ኃይሎች መካከል ከፍተኛ ግጭት ተከስቷል።
አይኤችአር ዕለቱ በርካታ ሰዎች የተገደሉበት እጅግ የከፋ ቀን እንደነበር ገልጿል። በዚህም በመላ አገሪቱ 13 ተቃዋሚዎች መገደላቸውን አረጋግጧል።
"ማስረጃዎቹ እንደሚያሳዩት የጥቃቱ መጠን በየቀኑ እየጨመረ መጥቷል" ሲሉ የቡድኑ ዳይሬክተር ማህሙድ አሚሪ-ሞጋዳም ተናግረዋል።
ሄንጋው በበኩሉ ረቡዕ ምሽት በሰሜናዊው የጊላን ግዛት በኮሽክ-ኢ ቢጃር ሁለት ተቃዋሚዎች በጸጥታ ኃይሎች በጥይት መገደላቸውን አስታውቋል።
ለአብዮታዊ ጥበቃ ጋር ቅርብ የሆነው የኢራኑ ኦፊሴላዊ የዜና ወኪል ፋርስ ረቡዕ ዕለት ሦስት የፖሊስ መኮንኖች መገደላቸውን ዘግቧል።
ሁለቱ በደቡብ ምዕራብ በምትገኘው ሎርዴጋን ከተማ ውስጥ በነበሩ "ተቃዋሚ" ታጣቂዎች በጥይት መገደላቸውን እና ሦስተኛው ደግሞ "አመፅን ለመቆጣጠር በሚደረገው ጥረት" ቴህራን ውስጥ ተወግቶ ሕይወቱ አልፏል።
ሐሙስ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራን ባለሥልጣናት ተቃዋሚዎችን ከገደሉ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት እንደሚኖር በድጋሚ ተናግረዋል።
"ሰዎችን መግደል ከጀመሩ ክፉኛ እንደምንመታቸው አሳውቄአቸዋለሁ" ሲሉ ከሂዊት ሾው ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ወቅት ተናግረዋል።
የአሜሪካ የግምጃ ቤት ኃላፊ ስኮት ቤሴንት በበኩላቸው የኢራን ኢኮኖሚ "በቋፍ ላይ ነው" ብለዋል።
"[ፕሬዝዳንት ትራምፕ] ተቃዋሚዎችን የበለጠ እንዲጎዱ አይፈልጉም። ይህ የውጥረት ጊዜ ነው" በማለት ሐሙስ ዕለት በሚኒሶታ የኢኮኖሚ ክለብ ንግግር ሲያደርጉ ተናግረዋል።
የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ቀደም ሲል የጸጥታ ኃይሎች ሰላማዊ ተቃዋሚዎችን "በከፍተኛ ጥንቃቄ" እንዲይዙ ጥሪ አቅርበዋል። "ማንኛውም የኃይል ወይም የአስገዳጅ ባህሪ መወገድ አለበት" ሲሉ ተናግሯል።
የኢራኑ መንፈሳዊ መሪ ኻሜኒ ቅዳሜ ዕለት ባለሥልጣናት "ከተቃዋሚዎች ጋር መነጋገር አለባቸው" አለባቸው ቢሉም "ተቃዋሚዎችም በቦታቸው መቀመጥ አለባቸው" ብለዋል።
ተቃውሞው የተጀመረው ታህሳስ 28 ቀን ሲሆን ነጋዴዎች የኢራን መገበያያ ሪአል ምንዛሪ በድጋሚ በከፍተኛ ሁኔታ በመውደቁ ቁጣቸውን ለመግለጽ ወደ ቴህራን ጎዳናዎች በወጡበት ጊዜ ነበር።
ባለፈው ዓመት ሪአል ዝቅተኛ ደረጃ ላይ የደረሰ ሲሆን የኢራን የኑክሌር ፕሮግራም ማዕቀቦች በመንግስት አስተዳደር እና በሙስና የተዳከመውን ኢኮኖሚውን ተከትሎ የዋጋ ግሽበት ወደ 40 በመቶ አድጓል።
የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ተቃውሞውን ተቀላቅለው ወደ ሌሎች ከተሞች መስፋፋት ጀመሩ።















