አንድ ሰው የሞተበት የተቃዋሚዎች እና የፖሊሶች ፍጥጫ በኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ

የኬንያ ተቃዋሚው ፖለቲከኛ ራይላ ኦዲንጋ የኑሮ መወደድን እና ፖለቲካዊ ጥያቄዎችን መሠረት አድርገው ደጋፊዎቻቸው ዛሬ ሰኞ መጋቢት 11/2015 ዓ.ም. ለተቃውሞ አደባባይ እንዲወጡ ጠርተው ነበር።

በዚህም ምክንያት በተለይ በዋና ከተማዋ ናይሮቢ ምንም እንኳን የሳምነቱ የመጀመሪያ የሥራ ቀን ቢሆንም እንቅስቃሴዎች በእጅጉ ተቀዛቅዘዋል።

የኬንያ መንግሥት የተቃውሞ ሰልፉ ሕገወጥ እና ያልተፈቀደ ነው ቢልም፣ በተለያዩ የከተማዋ ክፍሎች ውስጥ በአንስተኛ ደረጃ ወደ ጎዳና የወጡ ተቃዋሚዎች ታይተዋል።

ፖሊስም ተቃዋሚዎችን ለመበተን ከፍተኛ ኃይል ያለው ውሃ እና አስለቃሽ ጋዝ የተጠቀመ ሲሆን፣ እስካሁን አንድ ሰው ከፖሊስ በተተኮሰ ጥይት መሞቱ ተዘግቧል።

የተቃዋሚ ፓርቲው መሪ ራይላ ኦዲንጋ ምንም እንኳን ፍርድ ቤት ክሳቸውን ውድቅ ቢያደርገውም ባለፈው ዓመት ነሐሴ የተካሄደው ምርጫ ተሰርቋል የሚለውን ክሳቸውን አሁንም እያቀረቡ ነው።

በተጨማሪም ሥልጣን ከያዘ ስድስት ወራትን ያስቆጠረው የዊሊያም ሩቶ መንግሥት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ ያለውን የኑሮ ውድነት መፍትሄ ሊያበጅለት አልቻለም በማለት ደጋፊዎቻቸውን ለአደባባይ ተቃውሞ ጠርተዋል።

በተለይ ኦዲንጋ ከፍተኛ ደጋፊ ባላቸው የናይሮቢ የድሆች መኖሪያ በሆነው ኪቤራ አካባቢ ፖሊሶች ከተቃዋሚዎች ጋር ተጋጭተዋል።

በማዕከላዊ ናይሮቢ የሚገኙ የንግድ ተቋማትም የፀጥታ ችግሩን በመፍራት ዝግ ሆነው አስከ እኩለ ቀን ድረስ የቆዩ ሲሆን፣ ፖሊስ ለተቃውሞ የወጡ ሰልፈኞችን በአስለቃሽ ጋዝ በትነዋል።

በማዕከላዊው የከተማዋ ክፍል ውስጥ በሚገኘው የኬንያታ ጎዳና ላይም አንዳንድ ተቃዋሚዎች በፖሊሶች ላይ ድንጋይ ሲወረውሩ ታይዋል።

በኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ እስከ እኩለ ቀን ድረስ የነበረውን ሁኔታ ከስር ያሉት ፎቶግራፎች በተዋሰነ ደረጃ ያሳያሉ።