ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
አቶ ጌታቸው ረዳ በመጀመሪያው ጋዜጣዊ መግለጫቸው ምን አሉ?
አቶ ጌታቸው አዲስ የተቋቋመውን የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደርን ለመምራት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ መሾማቸው ከተገለጸ ከአንድ ቀን በኋላ መቀለ ውስጥ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
በዚህም በክልሉ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ እና ዲሞክራሲያዊ ማሻሻያዎችን ለማካሄድ እንደሚሰሩ ያመለከቱት አቶ ጌታቸው ረዳ በጦርነቱ ወቅት ለተከሰቱ ችግሮች መፍትሄ ለመፈለግ እንደሚጥሩ ገልጸዋል።
በቀዳሚነት የሚመሩት ጊዜያዊ አስተዳደር በቀጣይ ስለሚያከናውናቸው ተግባራት የጠቀሱት ጊዜያዊው ርዕሰ መስተዳደር፣ በክልሉ ዘላቂ ሰላም ለማምጣት፣ የጦር ወንጀል ተጠያቂነትን ማረጋገጥ፣ በሌሎች ኃይሎች ተይዘዋል ስላሏቸው አካባቢዎች እንዲሁም ስለ ኤርትራ እና አማራ ኃይሎችም ተናግረዋል።
ላለፉት ሁለት ዓመታት ከፌደራሉ መንግሥት ጋር ወታደራዊ ግጭት ውስጥ የገባው “የትግራይ ሕዝብ ትግል ምክንያታዊ ነበር” ያሉት አቶ ጌታቸው፣ አሁን ወደ አዲስ ምዕራፍ ሊያሸጋግር የሚችል ሰላማዊ ትግል መጀመሩን ተናግረዋል።
በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለውን አለመግባባት በሰላምና በውይይት ለመፍታት “ተስፋ ሰጪ እርምጃዎች ተወስደዋል” ብለዋል አቶ ጌታቸው።
በጥቅምት 2013 ዓ.ም. ትግራይ ውስጥ ተቀስቅሶ ወደ ወደ አጎራባቾቹ የአፋር እና የአማራ ክልሎች ተስፋፍቶ በነበረው ጦርነት ለመቶ ሺዎች ሞት፣ ለአስር ሺዎች መቁሰል እና ለሚሊዮኖች መፈናቀል ምክንያት መሆኑ ይነገራል።
ጦርነቱ ባለፈው ጥቅምት 23/2015 ዓ.ም. በሁለተኛ ዓመቱ በፕሪቶሪያ እና በናይሮቢ በተደረጉ ስምምነቶች ዘላቂ የሆነ የተኩስ አቁም ስምምነት ከተደረሰ በኋላ፣ ላለፉት አራት ወራት የፌደራል መንግሥት እና የህወሓት መሪዎች በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ለመመስረት ሲንቀሳቀሱ ቆይተዋል።
ከአንድ ሳምንት በፊት የዘገየውን የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደርን እንዲመሩ ፓርቲያቸው ህወሓት የሰየማቸው አቶ ጌታቸው ረዳ፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጊዜያዊ መስተዳደሩን እንዲመሩ ከመሾማቸው አንድ ቀን በፊት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በህወሓት ላይ ተጥሎ የነበረውን የሽብርተኝነት ፍረጃ አንስቷል።
ስለ አስተዳደሩ ቀጣይ ተግባራት ምን አሉ?
ህወሓት ከሽብርተኝነት መዝገብ ውስጥ ስሙ ከተነሳ በኋላ የክልሉን ጊዜያዊ አስተዳደር እንዲያዋቅሩ አቶ ጌታቸው ረዳ ኃላፊነቱ ሲሰጣቸው፣ በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ኃይሎችን ውክልና የሚያረጋግጥ አሳታፊ አስተዳደር የማቋቋም እንደሚጠበቅባቸው ተገልጿል።
በዚህም መሠረት አቶ ጌታቸው ረዳ የሚመሠረተው ጊዜያዊ አስተዳደር ሁሉንም የሚያሳትፍ እና የትግራይን አቅም የሚሰበስብ እንዲሆን ጥረት ተደርጓል ብለዋል። ይህም በፕሪቶሪያው ስምምነት መሠረት ሁሉም አስተሳሰቦች ዕድል የሚያገኙበት አዲስ ፖለቲካዊ ለውጥ የሚያመጣ ልዩ ምዕራፍ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
“ይህ ለውጥ ብዙ ጉድለቶች ቢኖሩትም መቀልበስ፣ መቆም ወይም መደናቀፍ የለበትም። ይህ በተሻለ ሁኔታ እንዲጠናከር ሁሉም የትግራይ ተወላጅ ሊተጋ ይገባል፤ ህወሐት ለዚህ አዲስ ጉዞ እና ለውጥ አርአያነቱን እንደሚወጣ ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ” ብለዋል።
ጊዜያዊ አስተዳደሩ የሚቆይበት ጊዜ አጭር በመሆኑ የክልሉን የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚወስኑ ኃላፊነቶችን እንደሚሸከምም ጊዜያዊ ርዕሰ መስተዳደሩ ተናግረዋል።
አቶ ጌታቸው አክለውም የክልሉን ሕዝብ ሰላም እና ደኅንነት ማረጋገጥ ከጊዜያዊ አስተዳደሩ ዋና ተልዕኮዎች አንዱ መሆኑን አመልክተው፣ የሰላም ሂደቱ በአጭር እና በረጅም ጊዜ ሰላምን በማጠናከር፣ የጦርነቱ መንስኤዎችን በመፍታት የክልሉን ዘላቂ አገራዊ ጥቅም እና የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት ያረጋግጣልም ብለዋል።
በተጨማሪም የትግራይ ክልል የግዛት ሁኔታም በፕሪቶሪያው ስምምነት መሠረት ሕገ መንግሥታዊ በሆነ መንገድ እንዲፈታ መቀመጡን አቶ ጌታቸው አስታውሰዋል።
“ምዕራብ ትግራይ፣ ደቡብ ትግራይ፣ የሰሜን ምዕራብ ትግራይ አካል የሆነው ጸለምቲ ወደ ነበሩበት የቀድሞ ቦታቸው አለመመለሳቸው ብቻ ሳይሆን እየደረሰ ያለው መፈናቀል እና የዘር ማጥፋት አሁንም በግልጽ እየቀጠለ ነው።
“ከእነዚህ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ዜጎች በአስቸኳይ ወደ ቤታቸው መመለስ አለባቸው። ባለው ሕገ መንግሥት መሠረት የትግራይ መሬት የትግራይ ነው” ብለዋል።
በእነዚህ አካባቢዎች ዙርያ የሚነሱ ጥያቄዎችም በሰላማዊ እና ሕገ መንግሥታዊ በሆነ መንገድ መፈታት እንዳለባቸው በመግለጽ፣ “በሁለቱ ሕዝቦች መካከል ያለው ግንኙነት የሚያስከትለው መዘዝ ቀላል ስለማይሆን፣ የአማራ የፀጥታ ኃይሎች ይህንን ተረድተው የተጀመረውን ሰላም የሚያደፈርሱ ድርጊቶችን ከመፈጸም እንዲቆጠቡ አሳስባለሁ” ብለዋል።
በትግራይ ክልል ስላሉ ኃይሎች
ከትግራይ እንዲወጣ ግፊት ሲደረግበት የቆየው የኤርትራ ጦር ካለፈው ጥር ወር ጀምሮ ከተለያዩ የሰሜን ምዕራብ እና መካከለኛ ትግራይ አካባቢዎች ለቆ መውጣቱን ሲገለጽ ቆይቷል።
ሆኖም አሁንም የኤርትራ መንግሥት የኢትዮጵያ ሉአላዊ ግዛት ከሆነው መሬት [ከአብዛኛው የትግራይ አካባቢዎች] አልወጣም ሲሉ አቶ ጌታቸው ተናግረዋል።
በሰሜን ኢትዮጵያ ለሁለት ዓመታት በዘለቀው ጦርነት የኤርትራ ሠራዊት እና የአማራ ኃይሎች ከፌደራል ሠራዊት ጋር በመሆን ከትግራይ ኃይሎች ጋር ተዋግተዋል።
በጦርነቱ ውስጥ የተሳተፉ ሁሉም ኃይሎች በጦር ወንጀሎች እና በሰብአዊነት ላይ በተፈጸሙ ወንጀሎች ይከሰሳሉ፤ ነገር ግን ሁሉም ክሱን ውድቅ ያደርጉታል።
የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን በዚህ ሳምንት በጽህፈት ቤታቸው ባወጣው የ2022 የሰብአዊ መብት ሪፖርት ላይ “ሁሉም በሰሜን ኢትዮጵያ በጦርነት የተሳተፉ ኃይሎች የጦር ወንጀል ፈጽመዋል” ማለታቸው ይታወሳል።
አቶ ጌታቸው በሰጡት መግለጫም “የበለጠ ግፍ እና በደል እየተፈጸመ ነው። የፌደራል መንግሥት እና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በሕዝባችን ላይ የሚደርሰውን ስቃይ ለማስቆም እና የተሟላ ሰላም እንዲሰፍን የተቻለውን ሁሉ እንዲያደርጉ ጥሪዬን አቀርባለሁ” ብለዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ አቶ ጌታቸው በጦርነቱ ወቅት ለተፈጸሙ ወንጀሎች ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ እንደሚሰራ ተናግረዋል። በጾታዊ ጥቃት ሰለባ የሆኑ ሴቶችን መልሶ ለማቋቋም እና በክልሉ ኢኮኖሚያዊ ተሃድሶ ለመጀመር ፖለቲካዊ እና ዲሞክራሲያዊ ማሻሻያዎችን ለማምጣት እንደሚሰራም ተናግሯል።
ከአጎራባች ክልሎች እና ከአገራት ጋር ሰላማዊ ግንኙነት ለመፍጠር በትኩረት እንደሚሰራም አቶ ጌታቸው ገልጸዋል።
“ያለፈው አልፏል፤ ስለ ነገው እንድናስብ ለመጪው ትውልድ ተስፋ ሰጪ አሻራ መተው አለብን” በማለት፣ እነዚህን ተግባራት ከዳር ለማድረስ የትግራይ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ ዲያስፖራዎች እና የፖለቲካ ኃይሎች እንዲሳተፉም ጥሪ አቅርበዋል።
ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ሰላምን ለማስፈን ላደረገው ጥረት ምስጋናቸውን ያቀረቡት አቶ ጌታቸው፣ ለክልሉ መልሶ ግንባታ፣ ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ፣ የሰላሙን ሂደት የሚያደፈርሱ ኃይሎችን ለመግታት እና በተፈጸሙ ግፎች ዙሪያ ተጠያቂነት እንዲያረጋግጥ ጠይቀዋል።