ኮሮና ቫይረስ መጠሪያ ስሙን አገኘ

የዓለም ጤና ድርጅት ከፍተኛ ኃላፊዎች በኮሮና ቫይረስ የሚከሰተውን በሽታ ኮቪድ-19 ብለን ሰይመነዋል ሲሉ ተናገሩ።

በጄኔቫ ለተሰበሰቡት ጋዜጠኞች "ለበሽታው ስያሜ አግኝተንለታል፤ ኮቪድ-19 ተብሎ ይጠራል" ያሉት የዓለም ጤና ድርጅት የበላይ ኃላፊ የሆኑት ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ናቸው።

በአሁን ሰአት ቫይረሱ ከአንድ ሺህ በላይ ሰዎችን ሕይወት የቀጠፈ ሲሆን በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ደግሞ ተይዘዋል።

ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም የአለምመሪዎች ቫይረሱን ለመዋጋት በብርቱ እንዲታገሉ ጥሪ አቅርበዋል።

ኮሮና ቫይረስ በሽታው የሚገኝበት የቫይረስ ቡድን ስያሜ ሲሆን፣ የበሽታው የተለየ መጠሪያ አለመሆኑ ተነግሯል።

ዓለምአቀፍ የቫይረስ ታክሶኖሚ ኮሚቴ በሽታውን ሳርስ-ኮቪ-2 (SARS-CoV-2 ) ነው በማለት መለየቱ ተሰምቷል።

ተመራማሪዎች ይህንን ቫይረስ በጅምላ ስሙ በመጥራት ግርታን ከመፍጠር ስም እንዲወጣለት ሲወተውቱ፣ አክለውም ሀገራትን ለይቶ ማግለልም ሆነ መፈረጅ እንዲቀር ነበር።

ዶክተር ቴዎድሮስ ስለ ቫይረሱ ስያሜ በተናገሩበት መግለጫ ላይ " ለቫይረሱ ስያሜ ስንሰጥ የትኛውንም መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ የማይገልፅ፣ እንስሳትን፣ ግለሰብንም ሆነ ቡድንን የማይነካ እንዲሁም ለአጠራር ምቹ የሆነ እንዲሆንና ከቫይረሱ ጋር ግንኙነት ያለው እንዲሆን ጥረናል" ብለዋል።

" ስም በሽታውን ለመከላከል፤ ትክክል ያልሆነን ወይንም መገለልን የሚያስከትል ነገርን እንዳንጠቀም ይከላከላል። እንዲሁም ለወደፊቱ ኮሮና ቫይረስ እንደገና በወረርሽኝ መልክ ቢከሰት ወጥ የሆነ አጠቃቀም እንድንከተል ያግዘናል" ብለዋል።

አዲሱ ስያሜ"ኮሮና"፣ "ቫይረስ" እና "ዲዝዝ"(በሽታ) ከሚሉት ቃላት እንዲሁም ከተከሰተበት ዓመተ ምህረት 2019 የተወሰደ መሆኑ ታውቋል።

ኮሮና ቫይረስ ለመጀመሪያ ጊዜ መከሰቱ የተመዘገበው ባለፈው ሕዳር ወር እንደ ጎርጎሳውያኑ አቆጣጠር ዴሴምበር 31 2019 ዓ.ም መሆኑ ይታወቃል።

በአሁኑ ሰዓት በቻይና ብቻ 42 ሺህ 200 ሰዎች መያዛቸው የተመዘገበ ሲሆን በበሽታው የሞቱ ሰዎች ቁጥር በ2002-2003 ተከስቶ በርካቶችን ከገደለው የሳርስ ወረርሽኝ ይበልጣል።

ቻይና ኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን በአግባቡ አልያዙም ያለቻቸውን ከፍተኛ ባለስልጣናት ከሥልጣን አንስታለች። የሁቤይ ጤና ኮሚሽን የፓርቲው ጸሐፊ እንዲሁም የኮሚሽኑ የበላይ ኃላፊ ከሥራቸው ከተነሱት ባለስልጣናት መካከል ናቸው።

እነዚህ ከፍተኛ ሹማምንት በቻይና ከበሽታው ጋር በተያያዘ ከስልጣናቸው የተነሱ የመጀመሪያዎቹ ከፍተኛ ባለስልጣናት ናቸው።

የአካባቢው የቀይ መስቀል ምክትል ኃላፊም የመጣውን እርዳታ በአግባቡ ካለማድረስ ጋር በተያያዘ "ኃላፊነትን በተገቢው ሁኔታ አለመወጣት" በሚል ከሥራቸው ተሰናብተዋል።

በትናንትናው ዕለትም የኢትዮጵያ የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የኮሮናቫይረስ በሽታን ምልክት አሳይተው የነበሩ አስራ አራት ኢትዮጵያውያን ከላብራቶሪ ምርመራ በኋላ ነፃ መሆናቸው አስታውቋል።