የጆሃንስበርግ ከንቲባ ኸርማን ማሻባ በዘር ምክንያት ከሥልጣናቸው ለቀቁ

የፎቶው ባለመብት, Sunday Times/Gallo Images
በደቡብ አፍሪካ ውስጥ ዋነኛ ተቃዋሚ የሆነውና በታሪክ የነጮች ፓርቲ ብቻ የነበረው ዲሞክራቲክ አሊያንስ ከፍተኛ ኃላፊነት የነበራቸው የጆሃንስበርግ ከንቲባ ከሥልጣናቸው እንዲሁም ከፓርቲያቸው ራሳቸውን አግልለዋል።
ኸርማን ማሻባ ለባለፉት ሶስት አመታት የጆሃንስበርግ ከንቲባ ሆነው አገልግለዋል።
በፓርቲው ውስጥ ያለው ስር የሰደደ ችግር ራሳቸውን ከፓርቲ አባልነታቸው እንዲያስወግዱ እንዲሁም ከከንቲባ እንዳስለቀቃቸው አሳውቀዋል።
" ሃገሪቱ ውስጥ ባሉት የእኩልነት ጥያቄዎች ውስጥ ዘር ከፍተኛ ቦታ እንዳለው መወያየት ከማይፈልጉ ሰዎች ጋር በጭራሽ አብሬ መስራት አልችልም" በማለት በመልቀቂያቸው በሰጡት መግለጫ አትተዋል።
ውሳኔያቸውን ያፋጠነው ጉዳይ ደግሞ ሄለን ዚሌ የተባለች የፓርቲው ነጭ አባል ቅኝ ግዛትን በማሞገስ ከፍተኛ የሆነ ቁጣን ቀስቅሳ የነበረ ቢሆንም በሥልጣን ከፍ መደረጓ ነው።
"የሄለን ዚሌ ሹመትም የሚያሳየው ከኔ ተፃራሪ እምነት ያላቸው ሰው ድል እንዳደረጉ ነው" ብለዋል።
በፓርቲው ውስጥ የጥቁር ከንቲባ መመረጥ ገዢውን ኤኤንሲ በስልጣን ሊገዳደር ይችል ይሆን የሚሉ መላምቶች እንዲሰጥ አስችሎት ነበር።
በራሱ የውስጥ ፖለቲካ እየተበጠበጠ ላለው ገዥው ፓርቲ ኤኤንሲ ይህ የሚያስደስት ዜና ሆኖላቸዋል።
ኤኤን ሲ በአሁኑ ወቅት ደካማ ቢሆንም በሃገሪቱ ውስጥ ትልቁ የሚባለው ተቃዋሚ ፓርቲ ምንም ሳይመጣበት በራሱ እየተሸራረፈ መሆኑ ነው።
የዲሞክራቲክ አሊያንስ ጥቁር አባላት እንደሚያምኑት ፓርቲው ወደቀድሞው ሙሉ በሙሉ ነጭ የማድረግ አላማው እንደገፋበት አሳይ ነው ማለታቸውን የቢቢሲው ሚልተን ንኮሲ ከጆሃንስበርግ ዘግቧል።
"ለደሃ የቆመ" ፖሊሲያቸውም፣ ትችት እንዲሁም ማጣጣል እንዲሁም ትችት እንደቀረበበት ከንቲባው አስረድተው፤ ለደሃ የቆመ ማለትም ለጥቁሮች የቆመ መሆኑን ሚልተን ይናገራል።
ኸርማን ማሻበ የጨቋኙ አፓርታይድ ስርዓት ከተገረሰሰ በኋላ ከገዥው ኤኤንሲ ፓርቲ ውጭ የተመረጡ የመጀመሪያው ጥቁር ከንቲባ ናቸው።
ሙምሲ ማይማኔ የተባሉት ጥቁር ደቡብ አፍሪካዊ የዲሞክራቲክ አሊያንስ መሪ ተደርገው ሲመረጡ የደቡብ አፍሪካ ኦባማም ተብለው ተሞካሽተው ነበር።
ሙምሲ ማይማኔም ቢሆን ለፖለቲካ ህይወታቸው እየታገሉ ያለበት ወቅት ላይ ናቸው።
ሰኞ ዕለት በነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ ከሥልጣን ከለቀቁት ከንቲባ ጎን በመቆምና እጃቸውን ከፍ አድርገው በመያዝ "ጀግናየ ነህ፣ ጀግናየ ነህ" ብለዋል ።
የፓርቲው መሪ ሙምሲ ማይማኔም ዕጣ ፈንታ በሚቀጥለው አመት በሚደረገው የፓርቲው መሪዎች ጉባኤ የሚወሰን ይሆናል።
ነገሮች እንዴት በፍጥነት እየሄዱ እንዳሉ በማየት ግን እስከዛ ድረስ ይቆዩ ይሆን ወይ ለሚለው ዋስትና የለም።

የፎቶው ባለመብት, Foto24/Gallo Images
ምንም እንኳን የሁለቱ አመራሮች ወደ ሥልጣን መምጣት ፓርቲው በጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን ዘንድ ያለውን ተቀባይነት ከፍ ያደርገዋል ቢባልም የሄለን ዚሌ ወደ ከፍተኛ አመራር መምጣት ግንቦት ወር ላይ በነበረው ምርጫ እንዲያሽቆለል አድርጎታል።












