ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ሉሲን የምትቀድም የሰው ዘር ቅሪተ አካል በደቡብ አፍሪካ ተገኘች
ቀደምት የሆነች እና የተሟላች የሰው አፅመ ቅሪት በደቡብ አፍሪካ ተገኘች።
ትክክለኛ እድሜዋ አከራካሪ ቢሆንም የደቡብ አፍሪካ ተመራማሪዎች የ3.7 ሚሊዮን ዓመት እድሜ ባለፀጋ መሆኗን ተናግረዋል።
ይህ ማለት ደግሞ ከኢትዮጵያዊቷ ሉሲ ባለትንሽ እግሯ ሰው ከ500,000 ዓመት በፊት ኖራለች።
ሉሲ እና ባለትንሽ እግሯ ተመሳሳይ የሰው ዘር- አውስትሮፒቲከስ ቢሆኑም በዝርያ ግን ይለያያሉ።
ተመራማሪዎች በአፍሪካ የሰው ዘር መገኛ ከዚህ ቀደም ከሚታሰበው በተለየ ቦታ ተበትነው እንደሚገኙ ያሳያል ሲሉ ተናግረዋል።
በተጨማሪም የተለያዩ ዝርያዎች መኖራቸውንም ያመለክታል።
ባለትንሽ እግሯ በሰሜን ምእራብ ደቡብ አፍሪካ ስትርክፎንቴይን በሚባል ዋሻ በፕሮፌሰር ሮን ክላርክ ነው የተገኘችው።
ወጣት ሴት ልትሆን እንደምትችል እና በዋሻው ውስጥ ወድቃ ይሆናል ሲሉ ግምታቸውን አስቀምጠዋል።
"ትንሽ ሊሆን ይችላል፤ ነገርግን በጣም ጠቃሚ ነው። ምክንያቱም በአንድ ትንሽ አጥንት ነው የተጀመረው። እናም አመጣጣችንን ለማወቅ ይረዳል" ሲሉ ፕሮፌሰር ክላርክ ተናግረዋል።
ከዋሻው ውስጥ አጥንቱን ማውጣት አድካሚ ነበር። በተጨማሪም ቅሪተ አካሎቹ "በቀላሉ ተሰባሪ " "በተፈጥሯዊ በንብርብር አለት መሰል ነገር የተቀበሩ" ነበሩ ሲሉ ያስረዳሉ።
"ለቁፋሮው በጣም ትንንሽ እንደ መርፌ ያሉ መሳሪያዎችን ነው የተጠቀምነው። ለዛ ነው ረጅም ጊዜ የወሰደው" በማለት አክለዋል።