የ2018 የቢቢሲ ምርጥ አፍሪካዊ ተጫዋች፡ አምስት ዕጩዎች

መህዲ ቤናቲያ፣ ካሊዶ ኩሊባሊ፣ ሳድዮ ማኔ፣ ቶማስ ፓርቴይ እና ሞሐማድ ሳላህ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, ከግራ ወደ ቀኝ፤ መህዲ ቤናቲያ፣ ካሊዶ ኩሊባሊ፣ ሳድዮ ማኔ፣ ቶማስ ፓርቴይ እና ሞሐማድ ሳላህ

የ2018 የቢቢሲ ምርጥ አፍሪካዊ ተጫዋች ዕጩዎች ይፋ ሆነዋል።

የዘንድሮው ዕጩዎች መህዲ ቤናቲያ ከሞሮኮ፤ ካሊድ ኩሊባሊ ከሴኔጋል፤ ሳድዮ ማኔ ከሴኔጋል፤ ቶማስ ፓርቴይ ከጋና እንዲሁም ሞሐመድ ሳላህ ከግብፅ ናቸው።

ቅዳሜ ዕለት ይፋ የሆነው ውድድሩ፤ ለሁለት ሳምንታት ያህል ከቆየ በኋላ ኅዳር 23/2011 አሸናፊው ታውቆ ይጠናቀቃል።

አሸናፊው በቢቢሲ ወርልድ ሰርቪስ ጣቢያዎች ዓርብ ታኅሳስ 5/2011 ለሕዝብ ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።

አምስቱ ዕጩዎች የተመረጡት በአፍሪካውያን የእግር ኳስ አዋቂዎች ስብስብ በተሞላ ቡድን ነው።

የሊቨርፑሉ አጥቂ ሞሐመድ ሳላህ የአምናውን ውድድር ማሸነፉ አይዘነጋም፤ ጄይ ጄይ ኦካቻ፣ ማይክል ኢሴይን፣ ዲዲየር ድርግባ፣ ያያ ቱሬ አና ሪያድ ማህሬዝም ከአሸናፊ ተጫዋቾች የሚጠቀሱ ናቸው።

ዕጩዎች

የ31 ዓመቱ የጁቬንቱስ መሃል ተከላካይ ቤናቲያ ባለፈው ዓመት ለአራተኛ ተከታታይ ጊዜ የሊግ ዋንጫ ማግኘት ችሏል፤ ሁለት ከባየር ሙኒክ እና ሁለት ከጁቬንቱስ ጋር።

የናፖሊው ተከላካይ ኩሊባሊ 27 ዓመቱ ሲሆን አምና ቡድኑ ዋንጫ ለማግኘት ከጁቬንቱስ ጋር ባደረገው ትንቅንቅ የበኩሉን አስተዋፅኦ ሲወጣ ነበር፤ በዓለም ዋንጫው ከሃገሩ ሴኔጋል ጋርም ተሳትፎ አድርጓል።

የ26 ዓመቱ የሊቨርፑል አጥቂ ማኔ፤ ለሴኔጋል በዓለም ዋንጫ ተፋልሟል። በዓምናው ቻምፒየንስ ሊግ ሁለተኛ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኖ መጨረስም ችሏል።

የአትሌቲኮ ማድሪዱ የ25 ዓመት አማካይ ቶማስ ፓርቴይ በዲዬጎ ሲሞኒ ቡድን ውስጥ የቋሚነት ሥፍራውን ማስከበር የቻለ ተጫዋች ነው። በዓምናው የአውሮፓ ሊግ ፍፃሜም ተቀይሮ በመግባት ተጫዋቷል። ለሃገሩ ጋናም በቋሚነት እየተጫወተ የሚገኝ አማካይ ነው።

የዚህ ውድድር የአምናው አሸናፊ የሊቨርፑሉ የ26 ዓመት አጥቂ ሞሃመድ ሳላህ የፕሪሚየር ሊጉን ወርቃማ ዋንጫ ማግኘት ችሏል፤ 32 ጎሎችን በማስቆጠር። በ10 ጎሎች ደግሞ ከቡድን አጋሩ ሳዲዮ ማኔ ጋር የቻምፒየንስ ሊጉን ከፍተኛ ጎል አስቆጣሪ ማዕረግ በሁለተኛነት መጨረስ ችሏል።