በደቡብ አፍሪቃ የታክሲ ሾፌሮች ላይ በተፈፀመ ጥቃት ሕይወት አለፈ

የፎቶው ባለመብት, AFP/GETTY
ደቡብ አፍሪቃ ውስጥ የሚኒባስ ታክሲ አሽከርካሪዎችን ዒላማ ያደረገው ጥቃት ለ11 ሰዎች ሕይወት ማለፍ ምክንያት ሆኗል።
ከደቡብ አፍሪቃዋ ጉዋቴንግ ግዛት ወደ ጆሃንስበርግ እያሽከረከሩ የነበሩት ባለታክሲዎች ቅዳሜ ዕለት ማታ ነው ያልታሰበ አደጋ የደረሰባቸው።
ከሞቱት 11 ግለሰቦች በተጨማሪ አራት ክፉኛ የቆሰሉቱ የሥራ አጋራቸውን ቀብረው እየተመለሱ የነበሩ የታክሲ አሽከርካሪዎች ናቸው።
ፖሊስ ግድያው በምን እንደተነሳ "እስካሁን ያጣራሁት ነገር የለም" ያለ ሲሆን መሰል ጥቃቶች ግን አዲስ እንዳልሆኑ አልሸሸገም።
በተለምዶ 'ሚኒባስ' ታክሲ በመባል የሚታወቁት ተሽከርካሪዎች 55 ሚሊዮን ገደማ ለሚሆነው የደቡብ አፍሪቃ ሕዝብ ዋነኛ የትራንስፖርት አማራጭ ናቸው።
የፖሊስ አፈ ቀላጤ የሆኑት ብርጋድዬር ጄይ ናይከር ሁኔታውን ሲያስረዱ «ጥቃቱ እንደደረሰ መኪናው ውስጥ ከነበሩት ግለሰቦች 11 ሕይወታቸው ወዲያውኑ ያለፈ ሲሆን አራት ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸው አሁን ሆስፒታል ይገኛሉ» ብለዋል።
«አካባቢው መሰል የታክሲ አሽከርካሪዎችን ማዕከል ያደረግ ጥቃት ሲከስትበት የመጀመሪያው አይደለም፤ ቢሆንም ሁኔታውን አጣርተን ጥቃት አድራሾቹን ለመያዝ እየተረባረብን ነው» ሲሉም አክለዋል።
የቅዳሜው ጥቃት የደረሰው ጆሃንስበርግ ውስጥ ተፈፀመ ከተባለው አሰቃቂ ግድያ ማግስት መሆኑ ነገሩን አሳሳቢ አድርጎታል።
ኬፕ ታውን በተሰኘችው የደቡብ አፍሪቃ ከተማም ወርሃ ግንቦት ላይ በደረሰ ጥቃት 10 የሚኒባስ ታክሲ ሾፌሮች መገደላቸው ይታወሳል።















