ጊኒ በምዕራብ አፍሪካ የመጀመሪያውን በማርበርግ ቫይረስ የተያዘ ሰው አገኘች

የማርበርግ ቫይረስ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የጊኒ የጤና ባለሥልጣናት በምዕራብ አፍሪካ የመጀመሪያውን የሆነውን በማርበርግ ቫይረስ የተያዘ ሰው መገኘቱን አረጋግጠዋል።

ቫይረሱ በከፍተኛ ሁኔታ ተላላፊ የሆነና ኢቦላን ከሚያስከትለው ቫይረስ ጋር በተመሳሳይ ዝርያ ውስጥ ነው ተብሏል።

የማርበርግ የቫይረስ በሽታ ወደ ሰዎች የሚተላለፈው ከሌሊት ወፎች ሲሆን ከሰው ወደ ሰውም የሚተላለፈው በሰውነት ፈሳሾች አማካኝነት ነው።

ትኩሳት እና የደም መፍሰስ ችግርን የሚያመጣ ከባድ ገዳይ በሽታ መሆኑም ተገልጿል።

የዓለም ጤና ድርጅት ቫይረሱ ሳይዛመት "በጅምሩ መቆም አለበት" ብሏል።

በቫይረሱ ከተያዘው የተወሰዱ ናሙናዎች በአገሪቱ ላቦራቶሪዎች ውስጥ ተመርምረው የማርበርግ ቫይረስ እንዳለበት ተረጋግጧል። በቫይረሱ የተያዘው ግለሰብም ህይወቱ አልፏል።

የዓለም ጤና ድርጅት ባልደረባ የሆኑት ዶክተር ማትሺዲሶ ሞኤቲ ቫይረሱ በሰፊው የመሰራጨት አቅም እንዳለው ተናግረዋል።

በአሁኑ ወቅት ከግለሰቡ ጋር ንክኪ የነበራቸው ሰዎችን ለማግኘት ጥረት እየተደረገ ነው።

የቅርብ ጊዜ የኢቦላ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር በጊኒ እና በአጎራባች አገሮች ውስጥ ተዘርግተው የነበሩ ስርዓቶች የማርበርግ ቫይረስንም ከመዛመት ለመከላከል ተግባራዊ እየሆኑ ነው ተብሏል።