የአሜሪካ የተራድኦ ድርጅት በኢትዮጵያ የረሃብ አደጋ ስጋት መኖሩን አመለከተ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የአሜሪካው የተራድኦ ድርጅት ዩኤስ አይዲ በኢትዮጵያ የረሃብ ስጋት መኖሩን ገለፀ።
የዩናይትድ ስቴትስ የዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲ (ዩኤስአይዲ) መሪ እና የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ ጉዳይ ሚንስትር በነበራቸው የጋራ ውይይት ላይ በኢትዮጵያ የረሃብ ስጋት አለ ስለማለታቸው ድርጅቱ በድረገፁ ላይ አስፍሯል።
የዩኤስአይዲ መሪ ሳማንታ ፓወር ከዩኬው የውጭ፣ የኮመን ዌልዝና የልማት ጉዳዮች ሚኒስትሩ ዶሜኔክ ራብ ጋር በበይነ መረብ አማካይነት ሲወያዩ በኢትዮጵያና በየመን እየጨመረ ነው ስላሉት የረሃብ ስጋት መወያየታቸውን ዩኤስአይዲ አስታውቋል።
ባለስልጣናቱ ስለ አሜሪካና ዩናይትድ ኪንግደም ግንኙነት መጠናከርን፣ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን፣ የሴቶች ትምህርት፣ የሰብአዊ እርዳታ በጀትና የአየር ንብረት ለውጥን በተመለከተ መወያየታቸውንም ድረ ገፁ አትቷል።
ጨምሮም "እንደ በኢትዮጵያና የመን ባሉ አገራት እየጨመረ ስለመጣው የረሃብ ስጋት መክረዋል" ከማለት ውጪ በየትኛው የአገሪቱ ክፍል የረሃብ አደጋ ስጋት እንዳለ ያለው ነገር የለም።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም በትግራይ ያለው ሁኔታ "እጅግ አስከፊ" ነው ብለዋል።
ዋና ዳይሬክተሩ ሰዎች በትግራይ ክልል በረሀብ ምክንያት ሰዎች እየሞቱ ነው፤ የምግብ እጥረትም እየተስፋፋ ነው ብለዋል።
የዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ቴድሮስ አድኃኖም በጄኔቭ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ "በትግራይ ያለው ሁኔታ ምናልባት ቃሉ ከገለጸው አስከፊ የሚባል ነው። እጅግ አስከፊ ነው" ብለው 4 ሚሊዮን ተኩል ወይም 5 ሚሊዮን ሕዝብ የሰብአዊ ድጋፍ እንደሚፈልግ ገልጸዋል።
"91 ከመቶ የሚሆነው ሕዝብ የምግብ እርዳታን የሚጠባበቅ ነው። በርካታ ሰዎች በእርግጥም በረሃብ እየሞቱ ነው። አሳሳቢ የሆነ የተመጣጠነ ምግብ እጥረትም በስፋት አጋጥሟል" ብለዋል።
በትግራይ የተከሰተውን ግጭት ተከትሎ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች አስቸኳይ የምግብ እርዳታ እንደሚያሻቸው ሲገለጽ ቆይቷል።
በትግራይ ክልል "በርካቶች በረሃብ ምክንያት ለሞት ሊዳረጉ እንደሚችሉ" ባለፈው ጥር አንድ የመንግሥት ባለስልጣን መናገራቸውን ከእርዳታ ሠራተኞች ጋር ከተደረገ ስብሰባ ላይ ሾልኮ የወጣ ማስታወሻ ላይ ሰፍሮ መገኘቱ መዘገቡ ይታወሳል።
በፌዴራልና በክልሉ መንግሥት መካከል በተፈጠረ ግጭት ከገበያዎች የምግብ አቅርቦት መመናመን፣ በክልሉ ተከስቶ በነበረው የአንበጣ ወረርሽኝና በተያያዥ ምክንያቶች በርካቶችን ለአስቸኳይ የምግብ ርዳታ እንዳጋለጣቸው የተለያዩ ሪፖርቶች ጠቁመዋል።
የተባበሩት መንግሥታት ደርጅት ደግሞ በትግራይ 4.5 ሚሊዮን ሕዝብ አስቸኳይ የምግብ ርዳታ ያስፈልገዋል ብሎ ነበር።
የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ የሰብዓዊ እርዳታ ለዜጎች ለማቅረብ የተቻለውን ሁሉ ሲያደርግ መቆየቱን በተደጋጋሚ ገልጿል።
መንግሥት ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ርዳታ አቅራቢ ድርጅቶ በመላው ትግራይ ገብተው እንዲሰሩም ከመፍቀዱም በላይ በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ሰዎች ድጋፍ ማድረጉን አስታውቋል።














