ሕዋ ሳይንስ፡ ከቁጥጥር ውጪ የሆነ ግዙፍ የቻይና ሮኬት ወደ ምድር እየተምዘገዘገ ነው

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ቻይና በቅርቡ ወደ ሕዋ ያስወነጨፈችው ሮኬት ከቁጥጥር ውጪ ሆኖ ቅዳሜ እና እሁድ ላይ ስብርባሪው መሬት እንደሚደርስ ተነገረ።
ይህ ከቁጥጥር ውጪ የሆነ የሮኬት ስብርባሪዎች አካል በትክክል መቼ እና የት እንደሚወድቁ እርግጠኛ መሆን አልተቻለም።
'ማርች 5ቢ' የሚል ስያሜ የተሰጠው ሮኬት ባሳለፍነው ወር መገባደጃ ላይ ነበር ቻይና በሕዋ ላይ ለመስራት ላሰበችው ማዕከል የሚሆኑ ቁሳቁሶችን ይዞ ነው ወደ ህዋ የተወነጨፈው።
18ሺህ ኪሎ ግራም የሚመዝነው ሮኬት በአስርት ዓመታት ውስጥ ቁጥጥር ሳይደረግበት ወደ ምድር የሚወድቅ ግዙፍ ቁስ ይሆናል ተብሏል።
አሜሪካ ትናንት ባወጣችው መግለጫ የሮኬቱን አቅጣጫ እና አካሄድ በቅርበት እየተከታተለች እንደሆነ በመግለጽ ተኩሳ የመጣል እቅድ ግን እንደሌላት አስታውቃለች።
የአሜሪካ የመከላከያ ሚንስትሩ ሎይድ ኦስቲን "ሮኬቱ ጉዳት ሳያስከትል እንደሚወድቅ ተስፋ እናደርጋለን" ብለዋል።
ምናልባት የባህር አካል ላይ ወይም ሰዎች በማይኖሩበት ቦታ ላይ ይወድቃል ብለው እንደሚገምቱ ተናግረዋል።

የመሬት አካል አብዛኛው ክፍል በውሃ የተሸፈነ እና አብዛኛው የምድራችን ክፍል ሰዎች የማይኖርበት መሆኑን ከግምት በማስገባት ሮኬቶ በሰዎች ላይ ሊያደርስ የሚችለው ጉዳት አነስተኛ ነው ተብሏል።
ባለሙያዎች 75 ሜትር ቁመት ያለው ሮኬት ምድር ሳይደርስ አብዛኛው ክፍሉ ተቃጥሎ ሊያልቅ እንደሚችል ጠቁመዋል። ከፍተኛ ሙቀት መቋቋም የሚችሉ እና የማይቀልጡ የሮኬቱ አካላት እንደሚወድቁ ግን ይጠበቃል።
ሮኬቱ ወደ ምድር ቢያንስ በሰዓት 60 ኪሎ ሜትር እየምዘገዘገም እንደሚወርድ ይጠበቃል።
ከዚህ በፊት በተመሳሳይ አንድ የቻይና መንኩራኩር ስብርባሪ ከታሰበለት ጊዜና ቦታ ውጪ ወደ ምድር ከባቢ አየር በመግባት በአንዲት የአይቮሪ ኮስት የገጠር መንደር ውስጥ ወድቆ ነበር።
የቻይና ሕዋ ሳይንስ ኤጀንሲ እስካሁን የሮኬቱን ስብርባሪ መቆጣጠር ይቻላል ወይ በሚለው ላይ ምንም አይነት አስተያየት አልሰጠም።
ቻይና ከዚህ በኋላም ተጨማሪ 10 ተመሳሳይነት ያላቸው ሮኬቶችን ወደ ሕዋ ለማስወንጨፍ እቅድ ያላት ሲሆን የአውሮፓውያኑ 2022 ከመጠናቀቁ በፊት ደግሞ የራሷን የሕዋ ማዕከል ለመገንባት አቅዳለች።












