የአፍሪካ ሕብረት የሶማሊያው ፕሬዝደንት ሥልጣናቸውን ማራዘማቸውን ተቃወመ

የፎቶው ባለመብት, AFP
የአፍሪካ ሕብረት የሶማሊያው ፕሬዝደንት ሞሐመድ አብዱላሂ ፎርማጆ የሥልጣን ዘመናቸውን ማራዘማቸውን ተቃወመ።
ሕብረቱ ልዩ መልዕክተኛ ወደ ሞጋዲሾ በመላክ የፖለቲካ ውጥንቅጡን ለመፍትታ እንደሚሞክርም አስታውቋል።
የአፍሪካ ሕብረት ሰላምና ፀጥታ ምክር ቤት ለሰዓታት ዝግ ስብሰባ ካካሄደ በኋላ ነው የሶማሊያን ፖለቲካዊ ችግር እፈታለሁ ያለው።
ሐሙስ ዕለት ከተካሄደው ስብሰባ በኋላ የተለቀቀው መግለጫ ሁሉም በአገሪቱ ውስጥ ያሉ ፓርቲዎች በጠረጴዛ ዙሪያ እንዲመክሩ አሳስቧል።
ባለፈው የፈረንጆቹ ዓመት መስከረም የሶማሊያ ፌዴራል መንግሥትና ክልላዊ አስተዳደሮች እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲዎች መክረው ነበር።
በዚህ ውይይት ወቅት በሶማሊያ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ እንዲደረግ ተስሰማምተው ነበር።
ነገር ግን ባለፈው ሳምንት ፕሬዝደንት ፎርማጆ የሥልጣን ዘመናቸውን እንዲራዘም የሚያትት ረቂቅ አፅድቀዋል።
የፕሬዝደንቱ አወዛጋቢ ውሳኔ ከብዙዎች ዘንድ ተቃውሞ እንዲገጥማቸው አድርጓል።
ዩናይትድ ስቴትስ፣ ብሪታኒያ፣ የተባበሩት መንግሥታትና የአውሮፓ ሕብረት የፕሬዝደንቱን እርምጃ ከተቃወሙ መካከል ናቸው።
"የመስከረም 2020 ስምምነት ለወደፊቱ ሶማሊያ አዋጭ የሆነ ዕቅድ ይዟል። ይህም ተዓማናኒ ነፃ ምርጫ ማድረግ ነው" ይላል ሕብረቱ የለቀቀው መግለጫ።
የሰላምና ፀጥታ ምክር ቤት የሶማሊያ ፖለቲካዊ አመራሮች ነገሮች የበለጠ የሚያከሩ ድርጊቶች ከመፈፀም እንዲቆጠቡም አሳስቧል።
ምክር ቤቱ ይህ ሆነ ማለት የሶማሊያ፣ የአፍሪካ ቀንድና የመላው አፍሪካ ሰላም ደፈረሰ ማለት ነው ሲል በመግለጫ አትቷል።
የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ፀጥታ ምክር ቤት በዝግ ባካሄደው ስብሰባ በቻድ ስላለው ሁኔታም ቢመክርም ለጊዜው ምንም ዓይነት ውሳኔ ላይ አልደረሰም።
የቻዱ ፕሬዝደንት ኢድሪስ ዴቢ ከታጣቂዎች ጋር በተደረገ ውጊያ ሕይወታቸው ማለፉን ይታወሳል።
የአፍሪካ ሃገራት መሪዎች በዴቢ ቀብር ላይ ለመገኘት ወደ ቻድ እያመሩ ይገኛሉ።












