አንበጣ ፡ ኢትዮጵያ የአንበጣ መንጋን ለመቆጣጠር ምን ያህል አውሮፕላኖች አሏት?

የምሥራቅ አፍሪካ አገራትን በማዳረስ በተለይ የኢትዮጵያን ሰሜናዊና ሰሜን ምሥራቅ አካባቢዎችን ክፉኛ እያጠቃ የሚገኘውን ግዙፍ የበረሃ አንበጣ መንጋ ለመከላከል ከአየር ላይ ጸረ ተባይ መድኃኒት የሚረጩ ጥቂት አውሮፕላኖች ተሰማርተው ጥረት እየተደረገ ነው።
የአንበጣ መንጋው ክፉኛ ባጠቃቸው አካባቢዎች የሚገኙ አርሶ አደሮች ብዙም ውጤታ ያልሆነውን ባህላዊ አንበጣን የመከላከያ መንገድ ጥረት እያደረጉ ሲሆን፤ ከዚሁ ጎን ለጎን አውሮፕላኖችም ተሰማርተው ጸረ ተባይ መድኃኒቶችን እየረጩ ቢሆንም እክል እየገጠማቸው የመከላከሉ ሥራ ላይ እክል እያጋጠመ ነው።
ባለፈው የመስከረም ወር ሁለት የጸረ ተባይ መርቻ አውሮፕላኖች በሰሜንና በምሥራቅ ኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ አካበቢዎች ተሰማርተው በነበረበት ጊዜ ወድቀው ከአገልግሎት ውጪ ሆነዋል።
የመጀመሪያው አውሮፕላን በአማራ ክልል ወረባቦ ወረዳ ፍራንጉል በሚባል ቦታ ወድቆ የተከሰከሰ ሲሆን የወረዳው የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ሳዳም ሽመልስ ለቢቢሲ እንደተናገሩት በአብራሪው ላይ ከደረሰው መጠነኛ ጉዳት ውጪ በሕይወት ላይ የደረሰ ጉዳት የለም።
ነገር ግን በአደጋው በአውሮፕላኑ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት የተነገረ ሲሆን በዚህም ሳቢያ አውሮፕላኑ ከአገልግሎት ውጪ ሊሆን ይችላል ተብሏል።
ሁለተኛው አውሮፕላን ደግሞ በኦሮሚያ ክልል በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን ጃርሶ ወረዳ የአንበጣ መንጋ ለመከላከል ኬሚካል በመርጨት ላይ በነበረበት ጊዜ ጊደያ በሃ በምትበል ቀበሌ ውስጥ ነው የመውደቅ አደጋ የገጠመው።
የወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አብዱል ቃድር ደዚ ለቢቢሲ በአደጋው ወቅት በአውሮፕላኑ ውስጥ አብራሪው ብቻ የነበረ ሲሆን እሱም ምንም አይነት ጉዳት እንዳልደረሰበትና በአውሮፕላኑ ላይም ቀላል ጉዳት እንዳጋጠመ ተናግረዋል።
ስለዚህም የአንበጣው መንጋ ጥፋት የሚያደርስባቸውን አካባቢዎች እያሰፋ ባለበት በዚህ ወቅት በአገሪቱ ውስጥ አሉ ከሚባሉት የጸረ አንበጣ መድኃኒት መርጫ አውሮፕላኖች ሁለቱ በአንድ ወር ውስጥ ከአገልግሎት ውጪ ሆነዋል ማለት ነው።
ለመሆኑ ኢትዮጵያ ስንት አውሮፕላኖች አሏት?
የአፍሪካ ቀንድንና ደቡብ እስያን እያካለለ ያገኘውን ሰብል በማውደም የአካባቢውን ሕዝብ የምግብ አቅርቦትና ህይወት አደጋ ላይ ጥሎ የሚኘውን በ25 ዓመት ውስጥ ካጋጠሙት ሁሉ የከፋው ነው የተባለለትን የአንበጣ መንጋ ወረርሽን ለመከላከል ኢትዮጵያ ከምድር እና ከአየር ጥረቶች ሲደረጉ ቆይተዋል።
የአንበጣ መንጋው ጥቃት ሰፊ ቦታን በሚሸፍን ቦታ ላይ እንደተከሰተ የግብርና ሚኒስቴር ግብርና ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ የሆኑት ማንደፍሮ ንጉሤ (ዶ/ር) የገለጹ ሲሆን፤ በአፋር፣ ሶማሊ፣ አማራ፣ ኦሮሚያና ትግራይ ክልሎችና በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የተለያዩ ወረዳዎች ውስጥ ተከስቷል።
ባለፉት ወራት በኢትዮጵያ ውስጥ የአንበጣ መንጋውን ለመከላከል ስድስት አውሮፕላን እና ሁለት ሄሊኮፕተሮች ተሠማርተው የነበሩ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት በገጠማቸው አደጋና ለጥገና ወደ ውጭ የሄዱ በመኖራቸው በሥራ ላይ የሚገኘው አንድ አውሮፕላን ብቻ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ለቢቢሲ ገልጸዋል።
የአንበጣ መንጋው በተከሰተባቸው አካባቢዎች ከዚህ ቀደም አውሮፕላኖቹ ተሰማርተው ባከናወኑት አንበጣውን የመከላከል ሥራ "በጣም ውጤታማ ነበሩ" የሚሉት ማንደፍሮ (ዶ/ር)፤ "በሰባት ክልሎች እና በአንድ ከተማ መስተዳድር የበረሃ አንበጣው ሲከሰት በተቀናጀ መልክ ተሠማርተው በመከላከል በሁለት ክልሎች ብቻ ሲቀር የሌሎቹን መቆጣጠር ችለው ነበር" ይላሉ።
ነገር ግን ከወራት በፊት የተከሰተውን የአንበጣ መንጋ በመቆጣጠር "የቀረውንም ተረባርበው ለማጥፋት ሲቃረቡ አዲስ የበረሃ አንበጣ መንጋ ከውጭ ገባ" የሚሉት ሚኒስትር ዲኤታው ሌላ ጫና መፈጠሩን አመልክተዋል።
ስለዚህም አሁን የተከሰተውን የበረሃ አንበጣ መንጋ ለመቆጣጠር በተደረገው ጥረት ውስጥ ሁለቱ እክል ገጥሟቸው የወደቁ ሲሆን ሌሎች ደግሞ በጥገና ላይ በመሆናቸው የቀረው አንድ አውሮፕላን ብቻ ነው።
ይህ ደግሞ በተለያዩ ክልሎች ውስጥ ካጋጠመው የአንበጣ መንጋ ወረራ አንጻር ከአቅም በላይ መሆኑን ጠቁመው፤ ለዚሁ ተግባር የሚውሉ አዳዲስ አውሮፕላኖች ባለፈው ሳምንት ማብቂያ ላይ ወደ ኢትዮጵያ ይገባሉ ተብሎ እየተጠበቀ መሆኑን ተናግረዋል።
አዲሶቹ የጸረ አንበጣ መድኃኒት መርጫ አውሮፕላኖች ስምንት ሲሆኑ የሚመጡትም በኪራይ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ማንደፍሮ (ዶ/ር) አመልክተው፤ ተባዩን ለመቆጣጠር በግብርና ሚኒስትሩ የሚመራ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ከአውሮፕላን በተጨማሪ በሰው ኃይልና በተሸከርካሪ በመታገዝ የጸረ ተባይ ርጭት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

አውሮፕላኖቹ ምን አጋጠማቸው?
የአንበጣ መንጋው ወረራ ከፍተኛ ደረጃ ላይ በደረሰበት ባለፈው የመስከረም ወር ላይ በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ውስጥ ጸረ አንበጣ መድኃኒት ለመርጨት ተሰማርተው የነበሩት አውሮፕኖች ላይ በተከታታይ የደረሰው አደጋ በአገሪቱ ውስጥ ያሉትን የጸረ ተባይ መርጫ አውሮፕላኖች ቁጥር አንድ ብቻ አድርጎታል።
ለአደጋው መከሰት ምክንያቱ ምን እንደሆነ የተገለጸ ነገር ባይኖርም ሚኒስትር ዲኤታው ማንደፍሮ (ዶ/ር) ግን "ከፍ ብሎ ለመብረር መቸገራቸው ምክንያት ሳይሆን አይቀርም" ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
አደጋው የደረሰባቸው ሁለቱም አውሮፕላኖች በኪራይ የመጡና ንብረትነታቸውም የደቡብ አፍሪካ ሲሆኑ፤ አብራሪዎቹም ኢትዮጵያዊያን አለመሆናቸው ተገልጿል።
አውሮፕላኖቹ የአንበጣ መንጋውን ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት እንዲያግዙ የመጡ ሲሆን የአደጋና የኢንሹራንስ ጉዳይ የግብርና ሚኒስቴርን የሚመለከት እንዳልሆነ ተጠቅሷል።
አደጋው መድረሱ እንዳሳዘናቸው ነገር ግን "እኛ በውላችን መሠረት ኪራይ መከፈል እንጂ አደጋ ሲደርስ እንከፍላለን የሚል ውል የለም" ሲሉ ማንደፍሮ (ዶ/ር) ተናግረዋል።
የግብርና ሚንስቴር የራሱ እንዲህ አይነቱ የተፈጥሮ ችግር በሚያጋጥምበት ጊዜ ፈጥነው በመሰማራት አገልግሎት ላይ የሚውሉ ሄሊኮፕተርም ሆነ አውሮፕላን እንደሌለው የጠቆሙት ሚንስትር ዲኤታው "አውሮፕላኖች ቢኖሩን ኖሮ አንበጣውን በፍጥነት ለመከላከል ይቻል ነበር" ብለዋል።
ከዚህ አንጻርም የጎረቤት አገር ሱዳን የግብርና ሚንስቴር የአንበጣ እና የወፍ መከላከያ እንዲሁም ለሌሎች ሥራዎች የሚያገለግሉ ዘጠኝ አውሮፕላኖች እንዳሉት ጠቅሰው በኢትዮጵያም "ተመሳሳይ አቅም መገንባት" አስፈላጊነትን ጠቅሰዋል።
ኢትዮጵያ ምን ያህል አውሮፕላኖች ያስፈልጓታል?
በተለይ በኢትዮጵያ ምሥራቃዊ ክፍል በሚገኙ ክልሎች ላይ ተከስቶ ከባድ ውድመት እያስከተለ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር ያመለከተውን የአንበጣ መንጋ ወራረ ለመከላከል ከአየር ላይ የሚደረገው የጸረ ተባይ ርጭት ወሳኝ መሆኑን ከዓለም የምግብ ፕሮግራም መረጃ ያመለክታል።
በተለይ ኢትዮጵያን በመሳሰሉ ተራራማ አገራት ውስጥ ከአየር ላይ የሚደረገው የጸረ አንበጣ መድኃኒት ርጭት አንበጣው የሚያደርሰውን ጉዳት በቶሎ ለመቆጣጠር ያስችላል። ነገር ግን አውሮፕላን ወይም ሄሊኮፕተር ለመግዛትም ሆነ ለመከራየት የሚያስፈልገው ገንዘብ ቀላል የሚባል አይደለም።
ሚኒስትር ዲኤታው እንደሚሉት አንድ ሄሊኮፕተር ለመግዛት የሚያስፈልገው ገንዘብ ሁለት ሚሊዮን ዶላር እንደሚገመት ጠቁመው፤ ኢትዮጵያ አስር ብትገዛ ወደ 20 ሚሊዮን ዶላር ወጪ እንደሚያስፈልጋት ተናግረዋል።
አንበጣው በአገሪቱ ግብርና ላይ ከሚያደርሰው ጉዳትና ለተለያዩ ችግሮች ከሚያጋልጣቸው የአገሪቱ ዜጎች አንጻር የአውሮፕላኖቹ አስፈላጊነት አጠያያቂ አይደለም ብለዋል ሚኒስትር ዲኤታው።
"በአገሪቱ ከዚህ በሚበልጥ ወጪ የሚሠሩ ፕሮጀክቶች መኖራቸውን እና በተመሳሳይ ለዚህም ግዢ ትኩረት ያስፈልጋል" ብለዋል።
አንድ አውሮፕላን የአንበጣ መንጋ በተከሰተባቸው አካባቢዎች በአንድ ጉዞ አንድ ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ኬሚካል የመርጨት አቅም ሲኖረው፤ አንድ አውሮፕላን በቀን እስከ አምስት ምልልስ በማከለናወን የጸረ አንበጣ መድኃኒት መርጨት ከቻለ አምስት ሺህ ሄክታር መሬትን መሸፈን ይችላል።
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ ከግማሽ ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በአንበጣ መንጋው የወረራ ስጋት ውስጥ ይሆናል ተብሎ እንደሚገመት ሚኒስትር ዲኤታው አመልከተው፤ ይህንንም ስፋት የጸረ ተባይ መድኃኒት ለመርጨት በትንሹ 10 አውሮፕላኖች ያስፈልጋሉ።
የበረሃ አንበጣ መንጋው እስካሁን ስላደረሰው ጉዳት ጥናት ባለመደረጉ የተረጋገጠ መረጃ አለመኖሩን የተናገሩት ማንደፍሮ (ዶ/ር) አሁን ዋነኛ ትኩረት የተደረገው በመከላከል ሥራው ላይ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል።
ሚኒስትር ዲኤታው ጨምረውም የበረሃ አንበጣውን ወረራ ለመከላከል ከአውሮፕላኖች በተጨማሪ በመቶዎች የሚቆጠሩ መኪኖች ጉዳቱ በከፋባቸው አካባቢዎች ተሰማርተዋል።
ከ25 ዓመታት ወዲህ የከፋ ነው የተባለለት የበረሃ አንበጣ ለወራት ኢትዮጵያን ጨምሮ በምሥራቅ አፍሪካ ያሉ አገራት ላይ ጉዳት እያደረሰ ነው።
ከባለፈው ዓመት ጀምሮ አስካሁን በተከታታይ ለተከሰተው የአንበጣ መንጋ ምክንያቱ እንደ አውሮፓዊያኑ በ2018 እና 2019 ያጋጠመው ከባድ ነፋስና ዝናብ እንደሆነ ባለሙያዎች ይናገራሉ።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መረጃ እንዳመለከተው ከሁለት ዓመት በፊት በደቡባዊ የአረብ ልሳነ ምድር ላይ የነበረው እርጥብና አመቺ የአየር ሁኔታ የአንበጣው ሦስት ትውልድ ሳይታወቅ እንዲራባ እድል ፈጥሮ በአካባቢው አገራት ላይ የሚታየውን የአንበጣ መንጋ ወረራ አስከትሏል።
















