ታዋቂው ሳኡዲ አረቢያዊው መብት ተሟጋች በእስር ቤት ሳሉ 'ህይወታቸው አለፈ'

ሰዎች በሪያድ ጎዳናዎች ላይ ሲራመዱ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

እአአ ከ2013 ጀምሮ በእስር ላይ የነበሩት የሳኡዲ አረቢያ ታዋቂ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች በእስር ቤት መሞታቸውን አክቲቪስቶች ተናገሩ።

ዶክትር አብዱላህ አል-ሃሚድ የሳኡዲ ሲቪል እና ፖለቲካ መብቶች ማኅበር መስራች የነበሩ ሲሆን በስትሮክ ተመተው በህይወት እና ሞት መካከል መቆየታቸው ተነግሯል።

የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች ዶ/ር አብዱላህ አል-ሃሚድ ከእስር እንዲለቀቁ በተደጋጋሚ ጫና ሲያሳድሩ ቆይተዋል።

በሰብዓዊ መብት አያያዝ የሚተቸው የሳዑዲ አረቢያ መንግሥት በአክቲቪስቱ የሞት ሪፖርት ላይ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥቧል።

የ69 ዓመት አዛውንት ከሆኑት ዶ/ር አብዱላህ አል-ሃሚድ ጋር ሞሐመድ አል-ቃሃታኒ የተባሉ አክቲቪስትም ለእስር ተዳርገው ነበር። ሁለቱ አክቲቪስቶች "አለመረጋጋትን በመፍጠር" ጥፋተኛ ተብለው እያንዳንዳቸው የ10 እና 11 ዓመት እስር ተበይኖባቸው ነበር።

የሳኡዲ አረቢያ የመብት ተሟጋቾች ዶ/ር አል-ሃሚድ በቂ የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ አልተደረገም ሲሉ የሳኡዲ አረቢያን መንግሥት ይተቻሉ።

ዶ/ር አል-ሃሚድ ካለፉት ሁለት ሳምንታት ወዲህ ጤናቸው መቃወሱ ተነግሯል።

መቀመጫቸውን ዩናይትድ ኪንግደም የደረጉት እና የሳኡዲ መንግሥት ተቺ የሆኑት መምህርት ማዳዊ አል-ራሺድ፤ ዶ/ር አል-ሃሚድን "የሰብዓዊ መብት ትግል ምልክት" ሲሉ ይገልጿቸዋል።

የሳኡዲ የሲቪል እና ፖለቲካል መብቶች ማኅበር መስራቾቹ ክስ ከተመሰረተባቸው በኋላ እንዲዘጋ ተደርጓል።