አሜሪካ በቂ የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ እንደሌላት ገለፀች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በመሃል አሜሪካ እንዲሁም ዳርቻዎች የኮሮናቫይስ ስርጭት እየጨመረ ቢሆንም አገሪቱ በቂ የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ መሳሪያ እንደሌላት ዋይት ሃውስ አምኗል።
ምክትል ፕሬዘዳንቱ ማይክ ፔንስ የትራምፕ አስተዳደር በዚህ ሳምንት ውስጥ ያስፈልጋል የተባለውን አንድ ሚሊዮን የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ መሳሪያ ማሟላት እንደማይችል በግልፅ ተናግረዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የአሜሪካ ኮንግረስ ኮሮናቫይረስን ለመከላከል ለሚደረገው እንቅስቃሴ የድንገተኛ እርዳታ በጀት ለማፅደቅ ባልተለመደ ሁኔታ እየተጣደፈ መሆኑ ተሰምቷል።
በትናንትናው እለት በአሜሪካ በኮሮናቫይረስ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 12 መድረሱም ታውቋል። በአሁኑ ወቅትም በመላ አገሪቱ 200 በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች በ20 ግዛቶች ውስጥ ተመዝግበዋል።
እስካሁን በዓለም አቀፍ ደረጃ 92 ሺህ የሚሆኑ ሰዎች በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሲሆን 80 ሺህ የሚሆኑት የበሽታው ክስተቶች የተመዘገቡት ቻይና ውስጥ ነው።
ሦስት ሺህ የሚሆኑ ሰዎች በቫይረሱ የሞቱ ሲሆን በተመሳሳይ አብዛኛው ሞት የተመዘገቡት ደግምኦ በቻይና ውስጥ ነው።
በዋሽንግተን የሲያትል ባለስልጣናት 20 የሚሆኑ በበሽታው የተያዙ ሰዎች መመዝገባቸውን፤ ይህ ደግሞ በአካባቢው በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 70 እንዳደረሰው ገልፀዋል።
ከሟቾቹ መካከል ዘጠኝ የሚሆኑት ሞቶች የተመዘገቡት በአንድ የአዛውንቶች መንከባከቢያ ማዕከል ውስጥ ነው። ማዕከሉ ትክክለኛውን የኮሮናቫይረስ መከላከያ መርህ እየተከተለ ለመሆኑ ምርመራ ተጀምሮበታል።
እንደ ማክሮሶፍትና አማዞን ያሉ የሲያትል አካባቢ ትልልቅ የቢዝነስ ተቋማት ቢሯቸውን በመዝጋት ሠራተኞች ከቤት እንዲሰሩ አድርገዋል።
በኒውዮርክ የተመዘገበው የኮሮናቫይረስ ቁጥር በአንድ ጀምበር ሁለት እጥፍ አድጎ 22 መድረሱም ተነግሯል። የከተማዋ ከንቲባም በአፋጣኝ በርካታ የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ መሳሪያዎች እንዲቀርቡላቸው ጠይቀዋል።
200 የሚሆኑ ሰዎች ደግሞ በጥርጣሬ በለይቶ ማከሚያ ውስጥ ይገኛሉ። በትናንትናው እለት ሳንፍራንሲስኮም የመጀመሪያውን በኮሮናቫይረስ የተያዘ ሰው አግኝታለች።












