ፊንላንድ በዓለም በእድሜ ትንሿን ጠቅላይ ሚኒስትር መረጠች

የሠላሳ አራት አመቷ የፊንላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ሳና ማሪን በዕድሜ የዓለም ትንሿ መሪ ሊሆኑ ነው።

በሴቶች የሚመራ ጥምረት መሪ የሆኑት ሳና ማሪን ጠቅላይ ሚኒስትር አንቲ ሪኔ መልቀቃቸውን ተከትሎ ነው ወደሥልጣን የመጡት።

የትራንስፖርት ሚኒስትር የነበሩት ሳና ማሪን በፓርቲያቸው ሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲ ነው የተመረጡት፤ በዚህ ሳምንትም ቃለ ሲመታቸውን ይፈፅማሉ ተብሏል።

በሴቶች የሚመራ የአምስት ፓርቲዎችንም ጥምረት ይመራሉ ተብሏል።

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አንቲ ሪኔ ስልጣን የለቀቁት የፖስታ ቤቶች ሰራተኞች የስራ ማቆም አድማን ተከትሎ ሁኔታውን የተቆጣጠሩበት መንገድ አንዳንድ የጥምረቱ አባላት መተማመን በማጣታቸው ነው ተብሏል።

በመቶዎች የሚቆጠሩ የፖስታ ቤት ሰራተኞችን ደመወዝ እቀንሳለሁ ማለታችውን ተከትሎ ሃገር አቀፍ የስራ ማቆም አድማ መትተዋል።

ሳና ማሪን ስልጣናቸውን ሲረከቡ የዓለም በዕድሜ ትንሿ ጠቅላይ ሚኒስትር ሲሆኑ፤ እስካሁን ባለው የጠቅላይ ሚኒስትሮች እድሜ የዩክሬኑ ጠቅላይ ሚኒስትር በሰላሳ አምስት አመታቸው፤ የኒውዚላንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጃሲንዳ አርደርን ደግሞ በ39 አመታቸው ይከተላሉ።

ጥምረቱ፤ ስልጣን ከተረከቡ በኋላ የነበረውን የሃገሪቱን ፕሮግራሙን እንደሚያስቀጥል ከመስማማቱ አንፃር አዲሷ ጠቅላይ ሚኒስትር ስር ነቀል የፖሊሲ ለውጥ ያመጣሉ ተብሎ አይታሰብም።

በጠባብ ልዩነት መንበረ ስልጣኑን ያሸነፉት ጠቅላይ ሚኒስትሯ ግን ሃገሪቷን በተለመደው መልኩ እንደማይመሩ አሳውቀዋል።

"የነበረውን እምነት ለመገንባት ከፍተኛ ስራ ያስፈልገዋል" በማለት ለሪፖርተሮች ተናግረዋል።

ከጋዜጠኞች እድሜያቸውን በተመለከተ ለቀረበላቸው ጥያቄም "እድሜዬም ሆነ ፆታዬ ትዝ ብሎኝ አያውቅም፤ ወደ ፖለቲካ የገባሁበትን ምክንያቶች ነው የማስበው፤ በነሱም ምክንያቶች ማሸነፍ ችለናል" ብለዋል።

አዲሷ ጠቅላይ ሚኒስትር ሳና ማሪን ያደጉት ያለአባት ሲሆን ዩኒቨርስቲም ሲገቡ ለቤተሰቡ የመጀመሪያ ናቸው ተብሏል።

በፓርቲያቸው ሶሻል ዲሞክራት የስልጣን እርከን በፍጥነት ወደላይ የወጡት ጠቅላይ ሚኒስትሯ በ27 አመታቸውም ታምፐሬ የምትባለው ከተማ አስተዳዳሪ ለመሆን በቅተዋል።

ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ስልጣን ከመምጣታቸው በፊትም የትራንስፖርትና ኮሚዩኒኬሽን ሚኒስትር ሆነው አገልግለዋል።