ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው ኢትዮጵያ ከኤርትራ የሚያደርጉት ጨዋታ አይካሄድም
የምስራቅና መካከለኛው አፍሪቃ የእግር ኳስ ውድድር ወይም በቅፅል ስሙ ሴካፋ ከቀጣዩ ቅዳሜ ጀምሮ በዩጋንዳ ይካሄዳል። በውድድሩ ምድብ ሀ ላይ የተመደቡት ኢትዮጵያ እና ኤርትራ እርስ በርስ ይገናኛሉ ተብሎ ተጠብቆ ነበር።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን እንደገለጸው የእግር ኳስ ቡድኑ አባላት ወደ ውድድሩ አይሄዱም።
ስለዚህ በርካቶች በጉጉት ሲጠብቁት የነበረው የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ብሄራዊ ቡድን አባላት የሚያደርጉት ግጥሚያ አይደረግም ማለት ነው። ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ከአዘጋጇ ኡጋንዳ እና ቡሩንዲ ጋር በአንድ ምድብ ተደልድለው ነበር።
ብሄራዊ ቡድኑ ለምን ወደ ኡጋንዳ እንደማይሄድ የጠየቅናቸው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን '' ምንም እንኳን የሴካፋ ውድድር ለብሄራዊ ቡድን ተጫዋቾች የሚፈሩበት ቢሆንም ከገንዘብ ጋር የተያያዘ ችግር ስላለብን ትልልቅ የሚባሉ የወዳጅነት ጨዋታዎች ላይ ወጪ ብናደርግ ይሻላል ብለን ወስነናል። በተጨማሪም ሊጉ ተቋርጦ ስለሆነ ውድድሩን የምንሳተፈው፤ ይህንን ከግምት ውስጥ አስገብተን ነው ውሳኔ ላይ የደረስነው'' ብለዋል።
አክለውም '' በርግጥ አወዳዳሪው አካል የሚሸፍነው ነገር ቢኖርም፣ ከ 15 ዓመት በታችና የሴቶች ብሄራዊ ቡድን ውድድሮች ላይ ተሳትፈን ነበር፤ ከዚህም ጋር በተያያዘ ያነሳናቸው የራሳችን ጥያቄዎች ነበሩ። በውድድሩም ያልተስማማንባቸው ነገሮች አሉ'' ብለዋል።
በሌላ በኩል በኡጋንዳ አዘጋጅነት በሚካሄደው የሴካፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን ውድድርም ኢትዮጵያ እንደማትሳተፍ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ አስታውቋል።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ከፊፋ እና ከካፍ ከሚያገኛቸው ድጋፎች እንዲሁም ከድጋፍ ሰጪ አካላት ከሚመጡ ገቢዎች ውጪ ምንም አይነት የበጀት ድጋፍ እንደማይደረግለት የገለጹት አቶ ጥላሁን ''ብሄራዊ ቡድን የትም ሲሄድ ወጪውን በሙሉ የሚሸፍነው ፌደሬሽኑ ነው፤ በዚህ ምክንያት እንቸገራለን በማለት ሁኔታውን ያስረዳሉ።
''ለካፍም ኢትዮጵያ በውድድሩ እንደማትሳተፍ ቀድመን በደብዳቤ አሳውቀናል።''
ኢትዮጵያና ኤርትራ በድንበር ምክንያት ጦርነት ውስጥ ከገቡ ጀምሮ በብሄራዊ ቡድን ደረጃ በየትኛውም ውድድር ተገናኝተው የማያውቁ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አሕመድ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ ግን ነገሮች ተቀይረዋል።
በርካታ የሁለቱም ሀገራት ደጋፊዎችም በውድድሩ የሁለቱን ሀገራት ብሄራዊ ቡድኖች ጨዋታ ለማየት በጉጉት እየተጠባባቁ ነበር። በኡጋንዳ ዋና ከተማ ካምፓላ የፊታችን ቅዳሜ ጀምሮ በሚካሄደው የሴካፋ ውድድር ሀገራት በሶስት ምድቦች ተከፍለው ይፋለማሉ።