በግድያ የተጠረጠሩት 22 ኢንች በምትሰፋ ቀዳዳ ሾልከው አመለጡ

የፎቶው ባለመብት, Monterey County Sheriff's Office
ፖሊስ በካሊፎርኒያ በአስደናቂ መልኩ ከእስር ቤት ያመለጡ ሁለት ተጠርጣሪዎችን ምስል ይፋ አደረገ።
ሳንቶስ ሳሙኤል ፎንሴካ እና ጆናታን ሳላዛር የ21 እና የ20 ዓመት ወጣቶች ሲሆኑ በግድያ ወንጀል ተጠርጥረው በእስር ላይ ይገኙ ነበር። ሁለቱ ተጠርጣሪዎች የእስር ክፍላቸውን ጣራ በመቦርቦር 22 ኢንች ስፋት ያለው ቀዳዳ ከፈጠሩ በኋላ ሾልከው አምልጠዋል።
"በግድያ የተጠረጠሩ ሰዎች ከእስር ቤት ውጪ መሆናቸው በጣም አሳዛኝ ነው" በማለት የአከባቢው ፖሊስ አዛዥ ጆናታን ቶርንበርግ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

የፎቶው ባለመብት, Monterey County Sheriff's Office
ባለሰልጣናት አደገኛ ናቸው፤ የጦር መሣሪያ ሳይታጠቁ አይቀርም የተባሉትን ሁለቱን ተጠርጣሪዎች ፍለጋ ላይ ይገኛሉ።
ፖሊስ ተጠርጣሪዎቹ የሚገኙበትን ለጠቆመ 5ሺህ የአሜሪካን ዶላር ሽልማት እንደሚሰጥ አስታውቋል።
ሁለቱ ተጠርጣሪዎች ከእስር ቤት ሊያመልጡ የቻሉት የእስር ቤቱ ጠባቂዎች ሊመለከቷቸው በማይችሉበት የመጸዳጃ ክፍል ጣሪያ በኩል ነበር።
21 ኢንች ብቻ ስፋት ያለው ቀዳዳ ሁለቱን ተጠርጣሪዎች ማሾለክ መቻሉን ፖሊስ ተናግሯል።

የፎቶው ባለመብት, Monterey County Sheriff's Office
ሁለቱ ተጠርጣሪዎች ከአንድ ዓመት በፊት ነበር በተለያዩ የግድያ ወንጀሎች ተጠርጥረው ነው በቁጥጥር ሥር የዋሉት።
ሳንቶስ ሳሙኤል ፎንሴካ ሁለት ሰዎችን በመግደል ተጠርጥሮ የታሰረ ሲሆን፤ ጆናታን ሳላዛር ደግሞ የ20 ዓመት ወጣትን ተኩሶ ገድሏል የሚል ክስ ነበር የቀረበበት ግለሰብ ነው።
ሁለቱም ተከሳሾች ጥፋተኛ አይደለንም ሲሉ እየተከራከሩ ነበር።












