ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ቦይንግ ከተሳፋሪዎች ደህንነት ትርፉን አስቀድሟል ተባለ
የአሜሪካ ሴናተሮች ኩባንያው የተሳፋሪዎችን ደህንነት ከማረጋገጥ ይልቅ ትርፉን አስቀድሟል ሲሉ ቦይንግን የወነጀሉት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈፃሙ ዴኒስ ሙለንበርግ ከሴኔቱ የንግድ ቋማ ኮሚቲ ፊት ቀርበው ነገሮቸን ባብራሩበት ወቅት ነው።
ሴናተሮቹ ኩባንያው ትርፉን ብቻ በማስላት ቦይንግን ቶሎ ወደ ስራ ለማስገባት መጣደፉ ከባድ ችግር ነበር ሲሉ ወቅሰዋል።
በአምስት ወር ልዩነት በደረሰው በላየን አየር መንገድና የኢትዮጵያ አየር መንገድ የቦይንግ ማክስ 8 አውሮፕላኖች አደጋ በጥቅሉ 346 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል።
ሴናተሮቹም ለሁለቱም አደጋዎች ምክንያት የሆነውን የአውሮፕላኑን ችግር ቦይንግ ቀደም ሲልም ያውቅ ነበር የሚለው ላይም በግልፅ ሃሳባቸውን አስቀምጠዋል።
ሴናተር ሪቻርድ ብሉሜንዛል እንዳሉት ቦይንግ ይሁንታን አግኝቶ ቶሎ ወደ በረራ እንዲገባ ኩባንያው ነገሮችን በጥድፊያ አድርጓል ሲሉ ደምድመዋል።
ከአደጋው ምርመራ ጋር በተያያዘም ቦይንግ በተደጋጋሚ ሆን ብሎ መረጃዎችን ሲያሳስትና ሲዋሽ እንደነበርም ገልፀዋል።