ኢትዮጵያ እና ኬንያ ድንበር ላይ በተከሰተው የጎርፍ አደጋ የሁለት ሰዎች ህይወት አለፈ

ኢትዮጵያ እና ኬንያ ድንበር ላይ በከባድ ዝናብ ሳቢያ በተከሰተው የጎርፍ አደጋ ለሁለት ሰዎች እና ለበርካታ የቤት እንስሳት ሞት ምክንያት ሆነ።
መርሰቢት በሚባለው የኬንያ ግዛት ውስጥ የድርቅ መከላከል ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑት ጉዮ ጎሊቻ ከዚህ ቀደም በአከባቢው በከባድ ዝናብ ሳቢያ የሚደርስ የጎረፍ አደጋ የተለመደ ቢሆንም የዘንድሮው ግን የተለየ ነው ብለዋል።
በጎርፉ አደጋ የሁለት ሰዎች ህይወት ማለፉንና ወደ 9 ሺህ የሚጠጉ የቤት እንስሳት መሞታቸውን አቶ ጎዮ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

"ከዝናብ በኋላ የተከሰተው ጎርፍ ከኢትዮጵያ ከሚመጣው ውሃ ጋር ተጨምሮ በሶሎሎ፣ ጎልቦ እና ዋጂራ ተብለው በሚጠሩ አከባቢዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት አስከትሏል" ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
በጎርፍ አደጋው ጉዳት ለደረሰባቸው ሰዎች የሚያስፈልጓቸው ድጋፎች እየተደረጉላቸው እንደሆነ ጨምረው ተናግረዋል።
ወደ 6ሺህ የሚጠጉ ፍየሎች እና ከ3ሺህ በላይ ከብቶች ሳይሞቱ እንዳልቀሩ ግምት አለ የሚሉት አቶ ጉዮ፤ 200 እስከ 300 የሚሆኑ መኖሪያ ቤቶችም ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰ ያስረዳሉ።
የቀይ መስቀል የመርሰቢት ግዛት ተወካይ የሆኑት ሞውሪስ አኒያንጎ "እስካሁን 226 ቤተሰብ መርዳት ችለናል" ያሉ ሲሆን የቀይ መስቀል እርዳታ ሰጪዎች በጎርፉ ሳቢያ እንደልብ በየብስ እየተንቀሳቀሱ እርዳታ መስጠት ስላልቻሉ በአየር ብቻ የተደረገፈ እርዳታ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።

"ከአሁን በኋላ እንኳ ለቀጣዮቹ ሁለት ወራት ዝናብ መዝነቡን ይቀጥላል። ተጨማሪ አደጋ ሊደርስ ስለሚችል ለህዝቡ የማስጠንቀቂያ መልዕክቶችን ማስተላለፍ ላይ ትኩረት አድርገውን እየሰራን ነው" ያሉት አቶ ጉዮ ናቸው።













