በካሊፎርኒያ ከተገደሉት መካከል የስድስት ዓመት ታዳጊ ይገኝበታል

በካሊፎርኒያ ''ግሎሪ ጋርሊክ'' በተሰኘ የምግብ ፌስቲቫል ላይ በደረሰ ጥቃት ቢያንስ ሶስት ሰዎች መገደላቸውንና 11 ግለሰቦች መቁሰላቸውን የአሜሪካ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

በፌስቲቫሉ በመጠናቀቂያ ላይ አንድ ታጣቂ ተኩሶ ከፍቶ ሰዎቹን ገድሏል ተብሏል።

ከሟቾቹ መካከል የስድስት ዓመቱ ታዳጊ ስቴፈን ሮሜሮ የሚገኝበት ሲሆን እናቱ እና አያቱ በጥቃቱ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

የስቴፈን አባት ሜርኩሪ ኒውስ ለተሰኘ መገናኛ ብዙሃን ሲናገር፤ ጥቃቱ ሲፈጸም እሱ ከ9 ዓመት ሴት ልጁ ጋር በመኖሪያ ቤቱ እንደነበረ እና ባለቤቱ በከፍተኛ ድንጋጤ ውስጥ ሆና እየተፈጸመ ያለውን ነገር በስልክ እንደነገረችው ያስታውሳል። "ልጃችን ከጀርባ በኩል በጥይት እንደተመታ ነገረችኝ" ሲል ተናግሯል።

ጥቃት አድራሹ ከፖሊስ ጋር የተኩስ ልውውጥ ካደረገ በኋላ መገደሉ ይፋ ተደርጓል።

የጥቃት አድራሹ ማንነት እስካሁን ይፋ ባይደረግም፤ በሰላሳዎቹ አጋማሽ እድሜ የሚገኝ ነጭ ግለሰብ ሲተኩስ እንዳየች ጁሊሳ ኮንትሪራስ የተባለች የአይን እማኝ ለኤንቢሲ ተናግራለች።

ሌሎች የዓይን እማኞች እንዳሉት ተኳሹ የወታደር ልብስ ለብሶ ነበር ብለዋል።

ፖሊስ ጥቆማው እንደደረሰን ከአንድ ደቂቃ ባነሰ ሰዓት በቦታው ደርሻለሁ ያለ ሲሆን፤ ከተኳሹ በተጨማሪ በጥቃቱ ላይ ረዳት ሆኖ የተሳተፈ ግለሰብ ስለመኖሩ መረጃው አለኝ ብሏል።

በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በተሰራጨ አንድ ቪዲዮም የፌስቲቫሉ ታዳሚዎች ሲሯሯጡ ታይቷል።

"ምን እየተካሄደ ነው? እንዴት የምግብ ፌስቲቫል ላይ ሰው ይተኩሳል?" የምትልም ሴት ድምፅ በቪዲዮው ላይ ተሰምቷል።

የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሰዎች እንዲጠነቀቁ በትዊተር ገፃቸው መልእክት አስተላልፈዋል።

የግሎሪ ከተማ አስተዳደር ዲዮን ብራኮ ለአሜሪካ ሚዲያ እንዳሳወቁት ሶስቱ ግለሰቦች መሞታቸውን ነው።

አስራ አንዱ ግለሰቦች ደግሞ በአስጊ ሁኔታ ላይ መሆናቸውንና በህክምናም ላይ እንደሚገኙ የሳንታ ክላራ የጤና ማዕከል ቃለ አቀባይ አስታውቀዋል።