ቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላኖችን ማምረት ላቆም እችላለሁ ሲል አስጠነቀቀ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላኖች ወደ በረራ የሚመለሱበት ጊዜ የሚጓተት ከሆነ አውሮፕላኖቹን ማምረቴን አቆማለሁ ሲል አስጠነቀቀ።
ትናንት በ737 ማክስ አውሮፕላኖቹ መዘዝ በሩብ ዓመት ውስጥ ብቻ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ የ3.4 ቢሊየን ዶላር ኪሳራ እንዳጋጠመው ይፋ አድርጓል።
በተለያዩ ቀጠናዎች ከሚገኙ አየር ተቆጣጣሪዎች ጋር የሚደረገው ትንቅንቅ የሚቀጥል ከሆነ እና አውሮፕላኖቹን በአጭር ግዜ ውስጥ ወደ በረራ መመለስ ካልቻልኩ ማክስ 737 አውሮፕላኖችን ማምረቴን ሙሉ በሙሉ አቆማለሁም ብሏል።
ይሁን እንጂ የቦይንግ ኃላፊ ዴኒስ ሙለንበርግ በጥቅምት ወር አውሮፕላኖቹ ወደ በረራ እንደሚመለሱ ባለሙሉ ተስፋ ናቸው።
ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ ሲበር የነበረው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 737 ማክስ 8 ከተከሰከሰ በኋላ በመላው ዓለም አውሮፕላኖቹ እንዳይበሩ እገዳ ተጥሎባቸዋል።
የኢትዮጵያው አየር መንገዱ አውሮፕላን ከመከስከሱ አምስት ወራት ቀደም ብሎ የኢንዶኔዢያው ቦይንግ 737 ማክስ መከስከሱ ይታወሳል።
ለሁለቱ አውሮፕለኖች መከስከስ ምክንያት ዝርዝር ምረመራ እየተካሄ ሲሆን፤ የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርቶች እንዲሁም የአየር በረራ ደህንነት ባለስልጣናት አውሮፕላኖቹ ኤምካስ ተብሎ የሚጠራው መተግበሪያቸው ላይ እክል መኖሩን ጠቁመዋል።
ቦይንግ በኤምካስ ስርዓቱ ላይ ችግር እንዳለ አምኖ እሱን ለማስተካከል እየሰራ ይገኛል።
ከወራት በፊት ኩባንያ ሊቀመንበር ዴኒስ ሙለንበርግ ''. . . ለኤምካስ ሶፍትዌር ማስተካከያ ከተደረገለት በኋላ 737 ማክስ አውሮፕላን ወደ በረራ ሲመለስ በበረራ ደህንነታቸው አስተማማኝ ከሆኑ አውሮፕላኖች መካከል አንዱ ይሆናል'' ሲሉ ተናግረው ነበር።
ቦይንግ የኤምካስ ስርዓቱ እያሻሻለ እንደሚገኝ እና እስካሁንም 225 የፍተሻ ምስለ በረራዎችን ማድረጉን ገልጿል።
ሁለቱ 737 ማክስ አውሮፕላኖች ከተከሰከሱ በኋላ ቦይንግ በወር ያመርት የነበረውን 737 ማክስ ከ52 ወደ 42 መቀነሱን የኩባንያው ሊቀመንበር ለባለሀብቶች ተናግረዋል።
ኩባንያው የሚያመርተው አውሮፕላን ቁጥር በመቀነሱ፤ ግብዓት የሚሆኑ ቁሶች ዋጋ አብሮ ጨምሯል። 737 ማክስ አውሮፕላኖችም ከበረራ በመታገዳቸውና ለደንበኞቹ ማስረከብ ባለመቻሉ ላመረተው ምርት ገቢ መሰብሰብ አልቻለም።
በእነዚህ እና በሌሎች ምክንያቶች ኩባንያው በሶስት ወራት ውስጥ 3.4 ቢሊየን ዶላር ከስሯል።ስለ አደጋው እስካሁን የምናውቀው

















