ስፔን ውስጥ ከኮርማዎች ጋር በተደረገው ሩጫ ሦስት ሰዎች ተጎዱ

ሦስት ሰዎች የተጎዱበት ከኮርማዎች ጋር የተደረገ ሩጫ

የፎቶው ባለመብት, EPA

የምስሉ መግለጫ, ሦስት ሰዎች የተጎዱበት ከኮርማዎች ጋር የተደረገ ሩጫ

ከነውጠኛ ኮርማ ጋር ሲሯሯዙ የነበሩ ሦስት ሰዎች ከፍተኛ ጉዳት ደረሰባቸው።

በስፔን በሚካሄደው ከነውጠኛ ኮርማዎች ጋር የመሯሯጥ ዓመታዊው ሳን ፌርሚን ፌስቲቫል ላይ 2 አሜሪካዊያንና የስፔን ዜጋ ላይ ጉዳት መድረሱን ባለስልጣናት አስታወቁ።

በቀይ መስቀል ህክምና የተደረገላቸው በጠቅላላው ቀላል ጉዳት ያስተናገዱ ሰዎች ቁጥር ወደ 48 እንደሚጠጋ ባለስልጣናቱ ጨምረው አስታውቀዋል።

ፌስቲቫሉ እስከ የፊታችን እሁድ የሚቀጥል ሲሆን ከኮርማው ጋር መሯሯጡ ጠዋት ጠዋት ላይ ይካሄዳል።

በፌስቲቫሉ ላይ የሚሳተፉት ሰዎች ነጭ ልብስ እና ቀይ ስካረፍ በማድረግ በጠባብ ጎዳና ላይ ለ850 ሜትር ከበሬ ፊት በመሮጥ ለኮርማዎች ወደ ተከለለው ቦታ ድረስ ከኮርማው ጋር ይሯሯጣሉ።

በየቀኑ ስድስት ኮርማዎች ይለቀቃሉ በዚህም በርካቶች ጉዳት ይደርስል። ይህ ጥንታዊ ፌስቲቫል ከ1910 ጀምሮ ሲካሄድ የቆየ ሲሆን እስካሁን 16 ሰዎች በኮርማዎች ተወግተው ህይታቸው አልፏል።

ለመጨራሻ ጊዜ አንገቱ ላይ ተወግቶ ህይወቱ ያለፈው ዳኒኤል ሮሜሮ 2009 ላይ ነበር።

ትናንት ጉዳት ያስተናገደው የ46 ዓመቱ አሜሪካዊም አንገቱ ላይ እንደተወጋና ቀዶ ህክምና እንደተደረገለት አሶሺየትድ ፕሬስ ዘግቧል።

ከኮርማዎች ጋር ሩጫ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

በዚህ ፌስቲቫሉ ላይ ለመሳተፍ በርካቶች ከመላው የዓለማችን ክፍል ወደ ስፔን ያቀናሉ። ዕድሜው ከ18 ዓመት በላይ የሆነ ሁሉ በፌስቲቫሉ ላይ መሳተፍ የሚችል ሲሆን አብዛኛውን ጊዜ ተሳታፊ ሆነው የሚታዩት ግን ወንዶች ብቻ ናቸው።

ከኮርማዎች ፊት የመሯሯጥ ፌስቲቫል በእንስሳት መብት ተሟጋቾች ከፍተኛ ተቃውሞ ይቀርብበታል።