ክትባት ከየት ተነስቶ የት ደረሰ?
ምንም እንኳ ባለፉት ዘመናት ክትባቶች በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎችን ህይወት ቢታደጉም፤ በበርካታ ሃገራት ውስጥ ለክትባቶች ያለው አሉታዊ አመለካከት እየጨመረ መምጣቱን ባለሙያዎች ይናገራሉ። .
የዓለም ጤና ድርጅት ባለንበት የፈረንጆች ዓመት ውስጥ በምድራችን ለጤና ስጋት ናቸው ብሎ ከዘረዘራቸው 10 ነገሮች መካከል ለክትባት እየታየ ያለው ቸልተኝነት አንዱ ነው።
ክትባት እንዴት ተገኘ?
ክትባቶች ከመገኘታቸው በፊት ዓለም ለሰው ልጆች አደገኛ ቦታ ነበረች። በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች በየዓመቱ አሁን በክትባት በምንከላከላቸው በሽታዎች ሳቢያ ይረግፉ ነበር።
በ10ኛው ክፍለ ዘመን ቻይናዊያን የመጀመሪያውን የክትባት አይነት አግኝተዋል። በዚህም ጤናማ ሰዎችን በሽታ አምጪ ለሆኑ ተዋህሲያን በማጋለጥ በሽታን የመከላከል አቅማቸው እንዲገነባ ያደርጉ ነበር።
ከስምንት ክፍለ ዘመኖች በኋላ ብሪታኒያዊው ዶክትር ኤድዋርድ ጀነር ወተት አላቢዎች ቀለል ባለው የላሞች ፈንጣጣ ቢያዙም በአደገኛው የላሞች ፈንጣጣ ፈጽሞ እንደማይያዙ ተገነዘበ።
በወቅቱ ፈንጣጣ በከፍተኛ ደረጃ ከሰው ወደ ሰው የሚተላለፍ ገዳይ በሽታ ሲሆን ከተያዙት ሰዎች መካከል 30 በመቶውን ለሞት ይዳርግ ነበር። በህይወት የተረፉት ላይም መታወር ወይም የማይሽር ጠባሳን ይጥላል።
ሰዎች ምን ያህል በዚህ ሃሳብ እንደሚስማሙ ተጠይቀው ነበር።
ውጤቱን ለማወቅ የሚፈልጉትን ይምረጡ
አጠቃላይ ውጤቱ ስለሚጠጋጋ 100% ላይሆን ይችላል
ጥናቱ ሰዎች በተለያዩ የሳይንስ ርዕሶች ላይ ያላቸውን አመለካከት ጠይቋል። ለአምስት ቁልፍ ጥያቄዎች የተሰጡ ምላሾች "በሳይንስ ላይ ያለ እምነት" ከፍተኛ፣ መካከለኛ ወይም ዝቅተኛ በሚል ተመልክቷል።
- ከፍተኛ
- መካከለኛ
- ዝቅተኛ
- አስተያየት ያልሰጡ
- ከፍተኛ
- መካከለኛ
- ዝቅተኛ
- አስተያየት ያልሰጡ
ምንጭ፡ Source: Wellcome Global Monitor, Gallup World Poll 2018
ይቅርታ፤ ስለዚህ ሃገር መረጃ የለንም
ኢንተርኔት የለም፤ በድጋሚ ይሞክሩ
እ.ኤ.አ በ1796 ጀነር፣ በስምንት ዓመቱ ታዳጊ ጄምስ ፊሊፕስ ላይ አንድ ሙከራ አደረገ።
ሃኪሙ በላሞች ኩፍኝ ከተጠቃ ሰው ቁስል ላይ መግል በመውሰድ በልጁ ላይ አደረገ፤ ከዚያም ታዳጊው የበሽታውን ምልክቶች ማሳየት ጀመረ።
ታዳጊው ከበሽታው ከዳነ በኋላ የፈንጣጣ ተዋህሲያን ወደ ሰውነቱ እንዲገባ ቢደረግም በበሽታው ሳይያዝ ጤናማ ሆኖ ቆየ። ምክንያቱም የላሞቹ ፈንጣጣ የመከላከል አቅሙን እንዲያዳብር ስላደረገው ነው።
በ1998 (እአአ) ዶክተሩ ያገኘው ውጤት ይፋ ሲደረግ 'ቫክሲን' የሚለው የእንግሊዝኛው የክትባት አቻ ቃል ከላቲኑ ላም ከሚለው 'ቫካ' ተወስዶ ይፋ ሆነ።
ስኬቶቹ ምን ነበሩ?
ክትባት ባለፉት ዘመናት የሰው ልጅን ሲያረግፉ የነበሩ በርካታ በሽታዎችን በመከላከል በኩል ከፍ ያለ አስተዋጽኦን አበርክቷል።
በ1960ዎቹ የመጀመሪያው የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት ከመተዋወቁ በፊት 2.6 ሚሊዮን ሰዎች በበሽታው ምክንያት በየዓመቱ ይሞቱ ነበር። በአውሮፓውያኑ 2000 እና 2017 መካከል በነበሩት ዓመታት በዓለም ዙሪያ በኩፍኝ ምክንያት የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር በ80 በመቶ ቀንሷል።
ከጥቂት አስርታት በፊት በነበረው ጊዜ በፖሊዮ ምክንያት መራመድ አለመቻልና ሞት የሚሊዮኖች ተጨባጭ ስጋት የነበረ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ግን ፖሊዮ ከሞላ ጎደል ከዓለም ጠፍቷል።
ዘመናዊ ክትባቶች ከተዋወቁበት ጊዜ አንስቶ ሰዎች በክትባቶች ላይ ጥርጣሬ ነበራቸው።
ቀደም ሲል በርካቶች ክትባትን የማይፈልጉት ከሃይማኖታዊ አስተሳሰብ በመነሳት ነው፤ ምክንያታቸውም ክትባቶቹ ንጹህ አይደሉም ወይም ደግሞ የመምረጥ ነጻነታቸውን ስለሚጻረር እንደሆነ ይናገሩ ነበር።
በ1800ዎቹ ታማሚዎችን ለብቻቻው ለይቶ ማስቀመጥን የመሰሉ ሌሎች ተላላፊ በሽታዎችን የመከላከያ ዘዴዎችን መጠቀም አለብን የሚሉ ጸረ ክትባት ቡድኖች ብሪታኒያ እና አሜሪካ ውስጥ ብቅ ብቅ ማለት ጀመሩ።
በ1998 መቀመጫውን ለንደን ያደረገ አንድ ዶክተር ኩፍኝን፣ ጆሮ ደግፍንና ሩቢላን የሚከላከለውን አንድን ክትባት ከኦቲዝምና ከሌላ ህመም ጋር በሃሰት በማያያዝ አንድ ዘገባ ይፋ አድርጎ ነበር። በዚህም ሳቢያ ዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ የሚከተቡ ህጻናት ቁጥር ቀነሰ።
በ2004 (እአአ) ብቻ ዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ ይህንን ክትባቱን የወሰዱ ህጻናት ቁጥር 100 ሺህ ብቻ ነበር። ይህም በሃገሪቱ የሚከሰተውን የኩፍኝ በሽታ ተከታታይ በነበሩት ዓመታት እንዲጨምር አድርጓል።

የፎቶው ባለመብት, Science Photo Library
የክትባት ጉዳይ ፖለቲካዊ ገጽታንም ይዞ ነበር። የጣሊያን የሃገር ውስጥ ሚኒስትር ማቲዮ ሳልቪኒ ከጸረ ክትባት ቡደኖች ጋር ሕብረት ፈጥረው ነበር።
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ካለምንም ማስረጃ ኦቲዝምን ከክትባት ጋር አያይዘውት የነበረ ቢሆንም፤ በኋላ ላይ ግን ወላጆች ልጆቻቸውን እንዲያስከትቡ ጥሪ ሲያቀርቡ ነበር።
ከአንድ ሃገር ህዝብ ውስጥ ከፍተኛውን ቁጥር የሚይዘው ነዋሪ ክትባትን ካገኘ በሽታዎችን በመከላከል ለበሽታ ተጋላጭ የሆኑትንና ሊከተቡ የማይችሉትን ሰዎች ጭምር ከገዳይ በሽታዎች መከላከል ይቻላል።
በዚህ ዘዴ በሽታን ለመከላከል መከተብ ያለበት የሕዝብ ቁጥር እንደየበሽታዎቹ ይለያያል። ኩፍኝ ለመከላከል ከአጠቃላዩ ሕዝብ ከ90 በመቶው በላይ መከተብ ሲኖርበት ለፖሊዮ ደግሞ ከ80 በመቶው በላይ ክትባቱን ማግኘት አለበት።
ባለፈው ዓመት አሜሪካ ብሩክሊን ውስጥ የሚገኙ አይሁዳዊያን ክትባት ከኦቲዝም ጋር ግንኙነት እንዳለው የሚገልጽ ጽሑፍ አሰራጭተው ነበር። በዚህም ሳቢያ ይህ የማኅበረሰብ በአሜሪካ በአስርታት ውስጥ ካጋጠሙት የኩፍኝ ወረርሽኞች መካከል አንዱን አስተናግደዋል።
የእንግሊዝ አንድ ታዋቂ ሃኪም እንዳስጠነቀቁት በርካታ ሰዎች በማህበራዊ ሚዲያ ላይ ስለክትባቶች በሚወጡ የተሳሳቱ መረጃዎች እየተታለሉ ነው ብለዋል።
ነገር ግን የዓለም ጤና ድርጅት ባወጣው መረጃ መሰረት በዓለም ዙሪያ ህጻናት መውሰድ ያለባቸውን ክትባቶች የወሰዱ ቁጥር ብዙም ለውጥ ሳያሳይ 85 በመቶ ላይ ይገኛል። ድርጅቱ እንደሚለው ክትባቶች በየዓመቱ ከሁለት እስከ ሦስት ሚሊዮን የሚደርሱ ሞቶችን ያስቀራል።
ባለንበት ዘመን የሚከተቡ ሰዎች ቁጥር እንዲቀንስ ዋነኛ ምክንያት የሆኑት ግጭቶችና ዝቅተኛ የጤና አገልግሎት አቅርቦቶች ሲሆኑ፤ ከዚህ አንጻርም አፍጋኒስታን፣ አንጎላና ዲሞክራቲክ ኮንጎ በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ።
በአደጉት ሃገራት ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች በሽታዎች የሚያስከትሉትን ከባድ ጉዳት ስለዘነጉ ለክትባት ቸልተኝነት እየታየ ነው።