ትኩረት እየሳበ የመጣው የሴቶች እግር ኳስ የዓለም ዋንጫ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የዘንድሮው የሴቶች የዓለም ዋንጫ ከሌሎቹ ጊዜያት በተለየ ሁኔታ በርካታ መሻሻሎችን አድርጎ ዛሬ በፈረንሳይ ይጀመራል።
ውድድሩ በ1991 (እአአ) ከጀመረ ወዲህ በማስታወቂያ፣ በቴክኖሎጂና በሌሎች ነገሮች ጉልህ መሻሻልን በማሳየት የወንዶቹን ያህል እንኳን ባይሆንም ያለውን ሰሪ ልዩነት በተወሰነ ደረጃ በማጥበብ ይካሄዳል።
የሚከተሉት ስድስት ጉዳዮች የሴቶች የዓለም እግር ኳስ ዋንጫ ያሳየውን ዕድገት ያሳያሉ።
ተሳታፊዎችና ተመልካቾች
ከአራት ዓመታት በፊት ካናዳ ውስጥ በተካሄደው የዓለም ዋንጫ ላይ የተደረጉትን 52 ግጥሚያዎች 1.35 ሚሊዮን ሰዎች ተመልክተውታል።
የዓለም እግር ኳስ የበላይ አካል የሆነው ፊፋ፤ ፈረንሳይ የምታስተናግደው የዚህ ዓመቱ የሴቶች እግር ኳስ የዓለም ዋንጫ ውድድርን ከባለፈው ጋር ተመሳሳይ አሊያም የበለጠ ቁጥር ያለው ሰው ይመለከተዋል ብሎ ይጠብቃል። ጨምሮም በቴሌቪዥን ውድድሩን የሚመለከተው ሰው ቁጥር ከባለፈው የዓለም ዋንጫ ከፍ እንደሚልም አመልክቷል።
ይህ የሴቶች የዓለም ዋንጫ በ1995 (እአአ) ኖርዌይ ውስጥ ሲካሄድ እያንዳንዱን ጨዋታ በአማካይ 4500 ሰዎች ብቻ ነበር የተመለከቱት። በአጠቃላይ ውድድሩን የተመለከቱት ሰዎች ደግሞ ከ112 ሺህ ያህል ብቻ ነበሩ።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
አመቺና ተመራጭ የስፖርት አልባሳት
በዚህ ዓመቱ የሴቶች የዓለም እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር ላይ ከሌላው ጊዜ በተለየ ተጫዋቾቹ ለወንዶች የተዘጋጀ የስፖርት ትጥቅን ሳይሆን ለሴቶች ተብለው የተዘጋጁ ትጥቆችን ይለብሳሉ።
ለዚህም በውድድሩ ከሚሳተፉት 24 ብሔራዊ ቡድኖች መካከል የሦስተ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊዋን አሜሪካንን፣ አስተናጋጇን ፈረንሳይን፣ የአውሮፓ ሻምፒዮናን ኔዘርላንድስ እና ብራዚልን ጨምሮ 14 ቡድኖችን ስፖንሰር ያደረገው የስፖርት ትጥቆች አምራች ድርጅቱ ናይኪ ነው።
የድርጅቱ የምርምርና የዲዛይን ቡድን የሴት እግር ኳስ ተጫዋቾች ፍላጎትን ከግምት በማስገባት ረጅም ጸጉር ላላቸው በቀላሉ የሚለበስና የሚወልቅ ማሊያዎች እንዲሁም ሰውነትን የማያጋልጡ ነገር ግን እንቀስቃሴን የማይገድቡ ቁምጣዎችን አዘጋጅቷል።
የኔዘርላንድስ ቡድን ማሊያም የሃገሪቱ ወንድ እግር ኳስ ቡድን ተጫዋቾች ደረት ላይ ይደረግ የነበረውን የወንድ አንበሳ ምስል በመቀየር ለሴቶቹ ምስሉ የሴት አንበሳ እንዲሆን ተደርጓል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ዝቅተኛ ክፍያ
የሴቶች እግር ኳስ ውድድር አሁንም ድረስ በገቢና በክፍያ በኩል ከወንዶቹ አቻቸው በእጅጉ ዝቅ ያለ ነው። ከሴቶች እግር ኳስ ተጫዋቾች መካከል ከፍተኛውን ክፍያ የምታገኘው የኖርዌይ ዜጋዋ አዳ ሄገርበርግ ስትሆን በዓመት የሚከፈላት 450 ሺህ ዶላር ነው።
ይህም ከአርጀንቲናዊው አጥቂ ሌዮኔል ሜሲ ጋር ሲነጻጸር በ325 እጥፍ ያነሰ መሆኑን ፍራንስ ፉትቦል የተባለው መጽሔት ያካሄደው ዓመታዊ ጥናት ያመለክታል።
የዚህ ዓመቱ የሴቶች የዓለም ዋንጫ ውድድር 30 ሚኒዮን ዶላር በሽልማት መልክ ለውድድሩ ተሳታፊዎች ይሰጣል። ይህም ቀደም ባለው ውድድር ላይ ከቀረበው እጥፍ ሲሆን በውድድሩ ታሪክም ከፍተኛው ነው።
ነገር ግን ለውድድሩ አሸናፊ ብድን 4 ሚሊዮን ዶላር የሚሰጥ ሲሆን ይህ በወንዶቹ ውድድር ላይ ከ16ቱ የዙር ፉክክር የሚሰናበቱ ቡድኖች ከሚያገኙት ገንዘብ ግማሹ ነው።
ይህ በወንዶችና በሴት እግር ኳስ ተጫዋቾች መካከል ያለው ሰፊ ልዩነት ኖርዌያዊቷ ሄገርበርግ ከዓለም ዋንጫ አራሷን እንድታገል አድርጓታል። ተጫዋቿ ከሀገሯ ብሔራዊ ቡድን ውጪ እንድትሆን ያደረጋትን ከፍ እያለ የመጠው ተስፋ መቁረጥና ለሴት እግር ኳስ ተጫዋቾች ያለው አክብሮት ዝቅተኛ መሆን ለውሳኔዋ ምክንያት እንደሆነ ገልጻለች።
በተመሳሳይ የአውስትራሊያ ሴት እግር ኳስ ተጫዋቾች ቅሬታቸውን ለፊፋ ያቀረቡ ሲሆን አሜሪካ ሴት እግር ኳስ ቡድን ተጫዋቾች ደግሞ በሚከፈላቸው ከወንዶች ያነሰ ክፍያ ምክንያት በሃገራቸው የእግር ኳስ ማህበር ላይ ክስ መስርተዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ሴት አሰልጣኞች
የአውሮፓ እግር ኳስ ውድድር የበላይ አስተዳዳሪ የሆነው ዩኤፋ እንደሚለው በአህጉሩ ካሉ የእግር ኳስ ቡድን የአሰልጣኝነት ሥራዎች ውስጥ 80 በመቶው በወንዶች የተያዙ ናቸው። በተጨማሪም 97 በመቶው የአሰልጣኝነት ፈቃድ የተሰጠው ለወንዶች ነው።
ከዚህ በመነሳትም በዚህ ዓመቱ የሴቶች እግር ኳስ ዋንጫ ከሚወዳደሩ 24 ብሔራዊ ቡድኖች መካከል ስምንቱ ሴት አሰልጣኞች አሏቸው። እነሱም ዋነኞቹን የውድድሩ ተፎካካሪዎች የሆኑትን ጀርመንና አሜሪካን መጨመሩ አውንታዊ ነው ተብሏል።
ብዙዎች እግር ኳስ መጫወት ይፈልጋሉ
በፊፋ ግምት መሰረት ከ30 ሚሊዮን የሚበልጡ ሴቶችና ልጃገረዶች በዓለም ዙሪያ እግር ኳስን ይጫወታሉ። ባለፉት አስር ዓመታትም በአማተርነት እግር ኳስን የሚጫወቱ ሴቶች ቁጥር ከ15 በመቶ በላይ በሆነ አሃዝ አድጓል።
ነገር ግን ይህ ቁጥር በዓለም ዙሪያ ከተመዘገበው እድገት አንጻር ከ10 በመቶ በታች ነው።
በዓለማችን ካሉ ሴት እግር ኳስ ተጫዋቾች መካከል ከግማሽ የሚበልጡት በአሜሪካና ካናዳ ውስጥ የሚገኙ ሲሆን ይህ በደቡብ አሜሪካ ላሉት መልካም ምሳሌ በመሆን ሊያነሳሳ ይችላል ተብሏል።
በወንዶች እግር ኳስ በዓለም ዙሪያ ስማቸው ዘወትር የሚነሱት የደቡብ አሜሪካ ሃገራት በሴቶች ዘርፍ ያላቸው ቁጥር ዝቅተኛ ነው። በደቡብ አሜሪካ ያሉት ሴት እግር ኳስ ተጫዋቾች ቁጥር ከ250 ሺህ በጥቂቱ አለፍ ያለ እንደሆነ የፊፋ መረጃ ያመለክታል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ፉክክሩ ከባድ ይሆናል
አሜሪካ ከዚህ በፊት የተካሄዱ ሦስት የሴቶች የዓለም ዋንጫን በማሸነፍና አራት የኦሎምፒክ ወርቅ ሜዳሊያዎችን በመውሰድ የውድድሩ ንግሥት ስትሆን፤ የዚህ ዓመቱን ዋንጫ ለማንሳት ትፎካከራለች። ቢሆንም ግን ተሳታፊ ቡድኖቹ በተቀራራቢ ደረጃ ላይ የሚገኙ በመሆናቸው ፉክክሩ ቀላል እንደማይሆን ይታመናል።
በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ ስፖርታዊ መረጃዎችን የሚሰበስበው ግራሴኖት የተባለው ድርጅት እንዳለው የዘንድሮውን የዓለም ዋንጫ ለማንሳት አዘጋጇ ፈረንሳይ በ 22 በመቶ ከፍተኛውን ግምት አግኝታለች።
የውድድሩ አሸናፊ ይሆናሉ ተብሎ ግምት ከተሰጣቸው መካከል አሜሪካ (በ14 በመቶ) የሁለት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ጀርምን (በ12 በመቶ) እና እንግሊዝ (በ11 በመቶ) እድል እንዳላቸው ተገምቷል።
ባልተጠበቀ ሁኔታ የውድድሩን ዋንጫ ያነሳሉ ተብለው የሚታሰቡት ደግሞ የወቅቱ የአውሮፓ ሻምፒዮን የሆኑት የኔዘርላንድ ሴት ብሔራዊ ቡድን አባላት ናቸው።












